የሀገር ውስጥ ዜና

ፋና 80 የውዝዋዜ ውድድር ለኪነጥበብ ዘርፉ ትልቅ እምርታ ነው – አቶ ነብዩ ባዬ

By Hailemaryam Tegegn

March 08, 2026

አዲስ አበባ፣ የካቲት 29፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ያዘጋጀው “ፋና 80” የዘመናዊና ባህላዊ ውዝዋዜ ውድድር ለኪነጥበብ ዘርፉ ትልቅ እምርታ ነው አሉ የባህልና ስፖርት ሚኒስትር ዴኤታ ነብዩ ባዬ፡፡

ፋና 80 የአሸናፊዎች አሸናፊ የፍፃሜ ውድድር እየተካሄደ ይገኛል፡፡

ሚኒስትር ዴኤታው በፍጻሜው ውድደር ላይ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት፥ ፋና 80 ወጣቶች አቅማቸውንና ክህሎታቸውን እንዲያዳብሩ እድል መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡

ከዚህ ቀደም ከሌሎች የጥበብ ይዘቶች ጋር በመሆን ይካሄድ የነበረውን የዳንስና ውዝዋዜ ውድድር ራሱን ችሎ መዘጋጀቱ ለጥበቡ ትልቅ እምርታ ነው ብለዋል

ለፍፃሜ የደረሱት ተወዳዳሪዎች በተለያዩ ዝግጅቶች ላይ እንዲሳተፉ እድሎች እንደሚመቻችላቸው ገልጸው፥ ለውድድሩ መልካም ምኞታቸውን ገልጸዋል፡፡

የፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈፃሚ አቶ አድማሱ ዳምጠው በበኩላቸው፥ ፋና 80 የኢትዮጵያ መታያ መልክ ነው ብለዋል ።

ይህን ያማረ ኢትዮጵያዊ መልክ ሁሉም በያለበት ሆኖ ኢትዮጵያን እንዲያውቃት በማድረግ የፋና 80 ድርሻ ጉልህ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

ውድድሩ አሁን ላይ በዳንስ ክህሎታቸውና የፈጠራ አቅማቸው እያስደመሙን ለሚገኙት ወጣቶች የመታያና ልምድ የመቀስሚያ ዕድል የፈጠረ መድረክ ነው ብለዋል።

በብርኽቲ ማህተመ