አዲስ አበባ፣ መጋቢት 30፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ሰባተኛው ሀገር አቀፍ የሰላም ኮንፈረንስ በአሶሳ ከተማ ይካሄዳል አለ የኢትዮጵያ ሐይማኖት ተቋማት ጉባዔ፡፡
የጉባዔው ጠቅላይ ጸኃፊ ሊቀ ትጉሃን ቀሲስ ታጋይ ታደለ በሰጡት መግለጫ እንዳሉት÷ የሰላም ኮንፈረንሱ “ሐይማኖቶች ለአንድነትና ለአብሮነት” በሚል መሪ ሃሳብ ሚያዚያ 7 እና 8 ቀን 2018 ዓ.ም ይካሄዳል፡፡
ኮንፈረንሱ ከቤኒሻንጉል ጉምዝ ክልል የሐይማኖት ተቋማት ጋር በመተባበር እንደሚዘጋጅ ተናግረዋል።
መርሐ ግብሩ በዋናነት እንደ ሀገር ያለውን ሰላም ማስቀጠል እንዲሁም የሐይማኖት መሪዎችና የሀገር ሽማግሌዎች የሰላም ምሳሌ የሆኑ ተግባራትን እንዲያከናውኑ ማስገንዘብ ላይ እንደሚያተኩር አስረድተዋል፡፡
በሰላም ኮንፈረንሱ ሕብረ ብሔራዊ አንድነትን ማጠናከር በሚያስችሉ ጉዳዮች ምክክር የሚደረግ ሲሆን÷ የፓናል ውይይቶች እንደሚከናወኑም አመልክተዋል፡፡
በአመለወርቅ መኳንንት