ዓለምአቀፋዊ ዜና

በእስራኤል የተጣለው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከነገ ጀምሮ ይነሳል

By Mikias Ayele

April 17, 2026

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 9፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ከሊባኖስ ጋር የተደረሰውን ስምምነት ተከትሎ እስራኤል ጥላው የነበረውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከነገ ጀምሮ ልታነሳ ነው፡፡

የእስራኤል ጦር እንዳስታወቀው ÷ የተኩስ አቁም ስምምነቱን ተከትሎ ከቅዳሜ ምሽት ጀምሮ በመላ ሀገሪቱ የወጣው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ይነሳል፡፡

ጦሩ በመካከለኛው ምስራቅ የተከሰተውን ጦርነት ተከትሎ በተጣለው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሀገሪቱ ዜጎች እንቅስቃሴያቸውን እንዲገድቡ እንዲሁም ት/ቤቶች እንዲዘጉ መደረጉ ይታወሳል፡፡

የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤኒያሚን ኔታንያሁ ÷ከሂዝቦላህ የአጭር ጊዜ እና የረጅም ጊዜ ስጋት ተጋርጦብን ነበር፤ነገር ግን በጦርነቱ ሁሉንም ስጋቶች አስወግደናል ብለዋል፡፡

ሂዝቦላህ ሰርጎ በመግባት በእስራኤል የሚፈፅመውን የሽብር ጥቃት ተከላክለናል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ ÷ ቡድኑ ይጠቀምባቸው የነበሩ ከ150 ሺህ በላይ ሚሳኤሎች መውደማቸውን አመልክተዋል፡፡

የቡድኑን ጥቃት ለመከላከል እስራኤል ከሊባኖስ ጋር በምትዋሰንበት ሰሜናዊ አቅጣጫ ወታደራዊ እንቅስቃሴ የማይደረገበት ነጻ ቀጣና እንዲካለል መደረጉንም ተናግረዋል፡፡

በሚኪያስ አየለ