አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 12፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በኢትዮጵያ እና በአውሮፓ ሕብረት መካከል ያለው ግንኙነት እየተጠናከረ መጥቷል አሉ የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር)።
ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) የአውሮፓ ሕብረት ዓለም አቀፍ አጋርነት ኮሚሽነር ጆሴፍ ሰኪላን በጽሕፈት ቤታቸው ተቀብለው አነጋግረዋል።
ሚኒስትሩ በዚህ ወቅት÷ ዛሬ የተጀመረው የአውሮፓ ሕብረት-ኢትዮጵያ ቢዝነስ ፎረም ውጤታማ መሆኑ አስደሳች መሆኑን ተናግረዋል።
በኢትዮጵያ እና በሕብረቱ መካከል ያለው ግንኙነት እየተጠናከረ መምጣቱን በማንሳት÷ የታዳሽ ኃይልን ጨምሮ በተለያዩ የኢንቨስትመንት ዘርፎች የሚደረገው ትብብር የበለጠ ሊጠናከር ይገባል ማለታቸውን የሚኒስቴሩ መረጃ አመላክቷል።
ኮሚሽነር ጆሴፍ ሰኪላ በበኩላቸው÷ በታዳሽ ኃይል መሠረተ ልማት፣ በዲጂታይዜሽን እና ሌሎች የትብብር መስኮች ሕብረቱ ከኢትዮጵያ ጋር ያለውን ትብብር አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል።