የሀገር ውስጥ ዜና

በሚዲያ ዘርፍ የተደረገው ሪፎርም ኢቢሲ ዓበይት የለውጥ እመርታ እንዲያሳይ በር ከፍቷል – አቶ ቢኒያም ኤሮ

By Adimasu Aragawu

May 07, 2026

አዲስ አበባ፣ ሚያዚያ 29፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የለውጡ መንግሥት በሚዲያው ዘርፍ ያደረገው ሪፎርም ኢቢሲ ዓበይት የለውጥ እመርታ እንዲያሳይ በር ከፍቷል አሉ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን ዋና ስራ አስፈጻሚ ቢኒያም ኤሮ፡፡

‎ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) በተገኙበት “የሚዲያ እመርታ ለትርክት ግንባታ” በሚል መሪ ሐሳብ ሀገራዊ የምክክር መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።

አቶ ቢኒያም ኤሮ በዚሁ ወቅት እንዳሉት÷ በኢትዮጵያ የዘመናዊ ሚዲያ ታሪክ ፈር ቀዳጁና የጥንቱ የኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን የነበሩበትን ዘርፈ ብዙ ተግዳሮቶች ለመፍታት የለውጡ መንግሥት በዘርፉ ያደረገው ሪፎርም ተቋሙ ዓበይት የለውጥ እመርታዎችን እንዲያሳይ በር ከፋች ነበር፡፡

መዋቅራዊ ክፍተቶች፣ ግልጽ ያልሆነ ኤዲቶርያል ፖሊሲ፣ የብዝኃነትና ተደራሽነት ፈተና እንዲሁም የቴክኖሎጂ ኋላቀርነት ተቋሙን የፈተኑት ማነቆዎች እንደነበሩ ገልጸዋል፡፡

‎ለውጡ እነዚህን ተግዳሮቶች ደረጃ በደረጃ ለይቶ በማረም ስኬቶችን አስመዝግቧል ነው ያሉት።

በርከት ያሉ ስቱዲዮዎችን በክልል ከተሞች ማስፋፋት፣ የዲጂታል ሚዲያ ተፎካካሪነትንና ዓለም አቀፍ የሚዲያ አጋርነትን ማጠናከር ላይ ሰፋፊ ስራዎች መሰራታቸውንም አስረድተዋል፡፡

በተጨማሪም የሀገርኛ ቋንቋዎችን በመጨመር ተደራሽነትን ማስፋት ከብዙ ጥቂቶቹ ስኬቶች ናቸው ማለታቸውን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት መረጃ አመላክቷል።