አዲስ አበባ፣ ግንቦት 6፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ዓለም አቀፍ የሙዚየም ቀንን ምክንያት በማድረግ ግንቦት 10 ቀን 2018 ዓ.ም ሁሉም ሙዚየሞች ለጎብኚዎች በነጻ ክፍት ይሆናሉ አለ የኢትዮጵያ ቅርስ ጥበቃ ባለስልጣን፡፡
ዓለም አቀፍ የሙዚየም ቀን “ሙዚየሞች የተከፋፈለውን ዓለም ያስተሳስራሉ” በሚል መሪ ሐሳብ በዓለም ለ49ኛ ጊዜ በኢትዮጵያ ደግሞ ለ24ኛ ጊዜ ይከበራል፡፡
የባለስልጣኑ ዋና ዳይሬክተር አበባው አያሌው እንዳሉት÷ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሀገራችን እየታየ ያለው የቱሪዝም ዘርፍ መነቃቃት በርካታ ሙዚየሞች እንዲገነቡ አስችሏል፡፡
ሙዚየሞች የጋራ የሆኑ እሴቶችን በማሳየት ልዩነቶችን ለማጥበብና የጋራ ትርክት ለመፍጠር ትልቅ ድርሻ እንዳላቸው ገልጸዋል፡፡
የዓድዋ ድል መታሰቢያ ዋና ዳይሬክተር ዮሴፍ ቤኮ (ዶ/ር) በበኩላቸው÷ የዓድዋ ድል መታሰቢያ በዓለም ላይ ካሉ ጥቂት የድል መታሰቢያዎች ውስጥ አንዱ መሆኑን ጠቅሰው ቀኑ ሲከበር አባቶቻችን በአንድነት እና በትስስር ያስገኙትን ድል በማስታወስ ሊሆን ይገባል ብለዋል፡፡
በመቅደስ የኔሁን