አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 28፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) በሳዑዲ ዓረቢያ በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ የነበሩ 1ሺህ 672 ኢትዮጵያውያንን ወደ ሀገራቸው መመለስ ተችሏል አለ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር፡፡ በሳምንቱ ውስጥ በተደረገ ስምንት ዙር በረራ ወደ ሀገራቸው ከተመለሱት ዜጎች መካከል እድሜያቸው ከ18 ዓመት በታች የሆኑ 34 ታዳጊዎች ይገኙበታል። መስከረም 5 ቀን 2018 ዓ.ም በተጀመረው ዜጎችን ወደ ሀገር ቤት የመመለስ ስራ እስካሁን ከ90 ሺህ በላይ ኢትዮጵያውያንን ወደ ሀገር መመለስ ተችሏል። በህገወጥ የሰዎች ዝውውር አስከፊነት ዙሪያ ህብረተሰቡን ለማስገንዘብ፣ መደበኛ ያልሆነ ፍልሰትን ለመከላከልና ደህንነቱ የተጠበቀ ፍልሰትን ለማበረታታት የሚያስችሉ ስራዎችን እየሰራ እንደሚገኝ አሳውቋል፡፡ መደበኛ ባልሆነ ፍልሰት ወደተለያዩ ሀገራት ሄደው የሚመለሱ የፍልሰት ተጎጂዎችን ለመደገፍና መልሶ ለማቋቋም በቅንጅት እየተሰራ መሆኑም ነው የተገለጸው፡፡ በቀጣይም ከባለድርሻ አጋር አካላት ጋር በመቀናጀት ለተመላሽ ዜጎች የሚደረገው ድጋፍና እንክብካቤ እንዲሁም ከቤተሰብ ጋር የማቀላቀል ስራ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ሚኒስቴሩ ገልጿል።