አዲስ አበባ – ነሐሴ 28፣ 2018 ዓ.ም (ኤፍ ኤም ሲ) መንግሥት የትምህርት ጥራት እና ፍትሃዊነትን ለማሻሻል ቀዳሚ አጀንዳው አድርጎ በትኩረት እየሠራ ነው አሉ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕስ መስተዳደር አሻድሊ ሀሰን። የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል 28ኛው ክልል አቀፍ የትምህርት ጉባኤ “ጥራትና ፍትሃዊነቱ የተረጋገጠ ትምህርት ለተሻለ የመማር ውጤት” በሚል መሪ ቃል እየተካሄደ ይገኛል።
በጉባዔው የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አሻድሊ ሀሰን፣ የኢፌዴሪ ትምህርት ሚኒስትር ብርሃኑ ነጋን(ፕ/ር) ጨምሮ የፌዴራል እና የክልል ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች እንዲሁም በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች ተገኝተዋል።
አቶ አሻድሊ ሀሰን በዚሁ ወቅት፣ ባለፉት ዓመታት በተለይም በትምህርት ተደራሽነት ላይ አበረታች ተግባራት ተከናውነዋል ብለዋል።
በተያዘው ዓመት በሀገር አቀፍ እና በክልል አቀፍ ፈተናዎች ላይ የተመዘገበው ውጤት መሻሻል ማሳየቱን አንስተዋል። አክለውም የትምህርት ጥራትን ለማሻሻል እየተደረገ ያለው ጥረት አሁንም ትኩረት ያስፈልገዋል ብለው ሁሉም ባለድርሻ አካል የበኩሉን መወጣት አለበት ሲሉ አሳስበዋል።
የትምህርት ሚኒስትር ብርሃኑ ነጋ(ፕ/ር) በበኩላቸው ባለፉት ዓመታት የተወሰዱ የትምህርት ዘርፉ ርምጃዎች ለውጥ እያስመዘገቡ ይገኛሉ ማለታቸውን የክልሉ ኮሙኒኬሽን መረጃ ያመለክታል።
ሚኒስትሩ እንደሀገር የተሻሻሉ የቅድመ መደበኛ፣ የአንደኛና የሁለተኛ ፣ እንዲሁም አዳሪ ትምህርት ቤቶች እየተገነቡ መሆኑንና በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልልም 36 የቅድመ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች እንደሚገነቡ አመልክተዋል።
ብርሃኑ ነጋ(ፕ/ር) በ2019 የትምህርት ዘመን ለሁሉም ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የኮምፒውተር ላብራቶሪ ለማሟላት እየተሠራ መሆኑንና 50 በመቶውን ኮምፒውተሮች ሚኒስቴሩ እንደሚሸፍንም አስረድተዋል።