አዲስ አበባ፣ ህዳር 30፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ እና የኬንያው ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ኢትዮጵያን ከኬንያ ጋር የሚያስተሳስረው የሞምባሳ-ናይሮቢ -አዲስ አበባ- ኮሪደር ግንባታ አካል የሆነው የሀዋሳ ሞያሌ መንገድ እና የጋራ የፍተሻ ጣቢያ ፕሮጀክት መርቀው ከፈቱ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ለሁለት ቀን ይፋዊ የስራ ጉብኝት ኬንያ ረፋድ ላይ መግባታቸው የሚታወስ ነው።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በሞያሌ የጋራ የፍተሻ ጣቢያ ሲደርሱ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ አቀባበል አድርገውላቸዋል።
የሞንባሳ ናይሮቢ አዲስ አበባ ኮሪደር ግንባታ አካል የሆነው እና የ500 ኪሎ ሜትር ርዝመት ያለው የሃዋሳ ሞያሌ መንገድ እና የሞያሌ የጋራ የፍተሻ ጣቢያ የሁለቱን ሀገራት ብሎም ቀጠናው በተለያዩ ዘርፎች በማስተሳሰር በኩል የጎላ ሚና ይኖረዋል ተብሏል።
የተመረቀው መንገድ 6 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ወጭ የተደረገበት ሲሆን ወጪው በአፍሪካ ልማት ባንክ የረጅም ጊዜ የብድር ድጋፍ የተሸፈነ መሆኑ ታውቋል።
መንገዱ በመስመሩ ለሚገኙ ከተሞች የእርሻ እና የኢንደስትሪ ዞኖች እና የቱሪስት መዳረሻወች በዘመናዊ መንገድ ከማስተሳሰሩ ባለፈ የኢትዮጲያ እና የኬኒያ መንግስት የሁለትዬሽ የንግድ ልውውጥ ግንኙነትን እንደሚያሳድግ ይጠበቃል።
በምንይችል አዘዘው