የሀገር ውስጥ ዜና

አሸባሪው ህወሃት የትግራይም ሆነ የመላው ኢትዮጵያውያን የጋራ ጠላት ነው – የአዲስ አበባ ሴቶች ማህበር ፕሬዚዳንት

By Meseret Awoke

July 22, 2021

አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 15፣ 2013(ኤፍ ቢ ሲ) ህወሃት የትግራይም ሆነ የመላው ኢትዮጵያውያን የጋራ ጠላት ነው ሲሉ የአዲስ አበባ ሴቶች ማህበር ፕሬዚዳንት ወይዘሮ ሁሉሃገርሽ ታዘዘ ገለጹ፡፡

የህወሃት ሽብር ቡድንን በመቃወም የሃገር መከላከያ ሰራዊትን የሚደግፍ ሰላማዊ ሰልፍ የአዲስ አበባ ሴቶችና ወጣቶች ማህበር አስተባብሯል፡፡

በዚህም የማህበሩ ፕሬዚዳንት ንግግር ያደረጉ ሲሆን፥ አሸባሪው የህወሃት ቡድን የኢትዮጵያን ሰላም ለማወክ ባለፉት አመታት ሲሰራ መቆየቱን አስታውሰዋል፡፡

ወይዘሮ ሁሉሃገርሽ እንደገለጹት፥ ቡድኑ የተዘረጋለትን የሰላም አማራጮች ሁሉ እየገፋ በሽብር ድርጊቱ በመዝለቅ ዛሬም የትግራይ ህዝብ የችግሩ ዋነኛ ገፈት ቀማሽ በማድረግ ለተጨማሪ ሰቆቃ እና መከራ እንዲጋለጥ አድርጎታል፡፡

ጁንታው የትግራይን ህዝብ በሃሰት ፕሮፓጋንዳው ከሌሎች ወንድም እና እህት ህዝቦች ጋር ለመለያየት እና ደም ለማፋሰስ እየሰራ ይገኛልም ብለዋል ፕሬዚዳንቷ፡፡

ህወሃት ሲነካ የትግራይ ህዝብ እንደተነካ አድርጎ፤ ህዝብንና አንድ ሽብርተኛ ቡድንን አንድ አድርጎ እና ህዝቡ ሌላ አማራጭ እንደሌለው ለማሳየት የሚሞክር አሸባሪ ቡድን መሆኑን ነው የገለጹት፡፡

ህወሃት የትግራይ ህዝብም ይሁን የመላው ኢትዮጵያውያን የጋራ ጠላት ነው ያሉ ሲሆን፥ የትግራይ ህዝብ ከመላው የኢትዮጵያውያን ወንድም እህቱ ጋር ኢትዮጵያን በመጠበቅ ሂደት በጋራ የተዋደቁ፣ አብሮ የኖረ እና ከሌሎች ህዝቦች ጋር ችግሩንም ደስታውንም በጋራ ያሳለፈ አንድ ህዝብ መሆኑንም ጠቁመዋል፡፡

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡- ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/ ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡ ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!