Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

በ6 ወራት በወንጀል ክርክር ሂደት 4 ሺህ 630 መዛግብት ክስ መቋረጡን ፍትህ ሚኒስቴር ገለጸ

አዲስ አበባ፣ ጥር 26፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) በግማሽ አመቱ በወንጀል ክርክር ሂደት ተከሳሶችና ምስክር ባለመቅረብ ምክንያት 4 ሺህ 630 መዛግብት ክስ መቋረጡን ፍትህ ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
ሚኒስቴሩ የ6 ወራት የስራ አፈጻጸም ሪፖርቱን ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤትአቅርቧል፡፡
በዚሁ ወቅት እንደተገለጸው ክሳቸው የተቋረጠ መዝገቦች ወንጀል ክርክር ከተደረገባቸው 26 ሺህ 257 መዝገቦች ውስጥ 4 ሺህ 630 መዛግብት ናቸው፡፡
ሪፖርቱን ያቀረቡት የፍትህ ሚኒትሩ ዶክተር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ በግማሽ አመቱ በድንበር ተሸጋሪ፣ በኢኮኖሚ፣ በሙስናና እና በልዩ ልዩ ወንጀሎች ላይ በተደረገ ክርክር በ8 ሺህ 389 መዝገቦች ላይ አቃቢ ህግ የፍርድ ውሳኔ ሲያሰጥ 96 ነጥብ 3 በመቶ የጥፋተኝነት ውሳኔ ተሰጥቷል ብለዋል፡፡

በወንጀል የተገኘ ሀብት ማስመለስን በተመለከተ በ6 ወር ብቻ 32 ሚሊየን 953 ሺህ 596 ብር ለመንግስት ገቢ መደረጉ በሪፖርቱ ተመላክቷል፡፡

ከመሬት ጋር በተያያዘም 2 ሺህ የሚሆን ካሬ እንዲወረስ ውሳኔ አግኝቶ መሬቱ ወደ መሬት ባንክ በመግባት ሂደት ላይ መሆኑ ተገልጿል፡፡

በሌላ በኩል በግማሽ አመቱ በተለያዩ ንብረቶች ላይ እግድ እንዲጣል ተደርጓል።

በዚሁ መሠረትም ስምንት ድርጅቶች በገንዘብ 1 ነጥብ 4 ቢሊየን 406 ብር፣ በሼር 32 ሚሊየን 516 ሺህ ብር፣ በተሽከርካሪ 233፣ በቤት 80 እና ማሽነሪ 114 ላይ እግድ ተጥሏል ፡፡

ከድርድር አፈጻጸም ጋር ተያይዞ በግማሽ አመቱ 25 መዛግብት ለድርድር ቀርበው ሁለት መዛግብት በስኬት መጠናቀቃቸው የተገለጸ ሲሆን፥ መዛግብቱ የያዙት የገንዘብ መጠንም አንደኛው 59 ነጥብ 6 ሚሊየን ብር ሲሆን÷ ሁለተኛው 87 ሺህ 494 የአሜሪካ ዶላር ነው ተብሏል፡፡

የግልግል ዳኝነት አፈጻጸም በሚመለከት በቀረበው ሪፖርት ከ11 ጉዳዮች በአንደኛው መዝገብ ኢትዮጵያ ከቀረበባት ክስ ነጻ መውጣቷ በሪፖርቱ የተገለጸ ሲሆን፥ ይህም የ300 ሚሊየን ዶላር መሆኑ ተመላክቷል፡፡

በሌላ በኩል በአሸባሪው ህወሓት ምክንያት በአማራ እና አፋር ክልሎች የተፈጸሙ ወንጀሎችን የሚያጣራ የምርመራ ቡድን በሁሉም ቦታዎች የወንጀል ምርመራ በማድረግ የተፈጸሙ ወንጀሎችን፣ ወንጀል ፈጻሚዎችን እና የወንጀሉን አፈጻጸም የማጣራት ስራ በመስራት የወንጀል ፈጻሚዎችን ተጠያቂ የማድረግ ስራ እየተከናወነ ነው ተብሏል፡፡

 

በሀይለየሱስ ስዩም

ኢትዮጵያን፦ እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
Exit mobile version