Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

የለሙ ቴክኖሎጂዎችና የተሰበሰቡ የሳተላይት መረጃዎች ተግባር ሊውሉ እንደሚገባ ቋሚ ኮሚቴው አሳሰበ

አዲስ አበባ ፣ ሚያዝያ 12 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የለሙ ቴክኖሎጂዎችና የተሰበሰቡ የሳተላይት መረጃዎች ተግባር ሊውሉ እንደሚገባ የሰው ሀብት ልማት ስራ ስምሪት እና ቴክኖሎጂ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ አሳሰበ፡፡
ቋሚ ኮሚቴው በኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩት የለሙ ቴክኖሎጂዎች እና መረጃዎች ወደ ተግባር እንዲለወጡ የግንዛቤ ማስጨበጥና የማስተዋወቅ ስራ መሰራት እንዳለበት አሳስቧል።
ቋሚ ኮሚቴው ሰሞኑን የእንጦጦ ኦቭዘርቫቶሪና ምርምር ማዕከልን ጎብኝቷል።
የቋሚ ኮሚቴው ምክትል ሰብሳቢ ዶክተር ከይረዲን ተዘራ በኢንስቲቲዩቱ ውስጥ የሚከናወኑ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ምርምር ተግባራት ያሉበት ደረጃ እና ማዕከሉ ወቅቱ የደረሰበትን የቴክኖሎጂ ሳተላይቶችን በመጠቀም እንዲሁም ለተለያዩ ተግባራት የሚውሉ መረጃዎችን በመሰብሰብ ጥቅም ላይ እንዲውሉ እያደረገ ያለው ጥረት የሚደነቅ መሆኑን ገልፀዋል።

በሳተላይት መረጃ መቀበያና መቆጣጠሪያ ጣቢያ የሚሰበሰቡት መረጃዎች ለሚፈለገው ተግባር እንዲውሉ የማስታወቂያና የግንዛቤ ማስጨበጫ ተግባራት በትኩረት መከናወን እንዳለባቸው አስገንዝበዋል፡፡

የኢትዮጵያ ስፔስ ሳይንስና ቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩት ዋና ዳይሬክተር አቶ አብዲሳ ይልማ÷ የማስተዋወቅ ተግባራትን ለማከናወን አዲስ እስትራቴጂ ተቀርጾ ከሚመለከታቸው ተቋማት ጋር በትብብር ለመስራት የጋራ ግብረ ኃይል በማቋቋም ሥራ መጀመሩን ተናግረዋል፡፡

ኢትዮጵያ ወቅቱ ከሚያመጣቸው ፈተናዎች አሸንፋ እንድትወጣና በቴክኖሎጂው ተጠቃሚ እንድትሆን ዘርፉን በቴክኖሎጂና በሰለጠነ የሰው ኃይል ማጠናከር እንደሚገባ መጠቆሙን ከሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

ኢትዮጵያን፦ እናልማ፣ እንገንባ፣ እንዘጋጅ!
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
Exit mobile version