አዲስ አበባ፣ ሰኔ 11፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢፌዴሪ ፍትህ ሚኒስትር ዶክተር ጌዲዮን ጢሞቴዎስ ከአውሮፓ ህብረት የሰብአዊ መብት ጉዳዮች ልዩ ተወካይ ኢሞን ጊልሞር ጋር በኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳዮች ዙርያ ተወያዩ፡፡
ዶክተር ጌዲዎን ከልዩ ተወካዩ ጋር በብራሰልስ ተገናኝተው በኢትዮጵያ ወቅታዊ ጉዳዮች ዙርያ ውይይት ማድረጋቸው ተገልጿል ፡፡
የአውሮፓ ህብረት ልዩ ተወካዩ በግንቦት ወር አዲስ አበባን ከጎበኙ በኋላ ሁለቱ ወገኖች በኢትዮጵያ ስላለው ወቅታዊ ሁኔታ መረጃ ይለዋወጡ እንደነበር ተጠቁሟል፡፡
ሚኒስትሩ በዋናነት በሰብአዊ መብት ጉዳዮች፣ በተጠያቂነት እና በአፍሪካ ህብረት መሪነት እየተካሄደ ባለው የሰላም ጥረት ላይ ስላሉ ትልልቅ ለውጦች ትኩረት ያደረገ ማብራሪያ ለተወካዩ አቅርበዋል፡፡
ተወካዩ በኢትዮጵያ አወንታዊ ለውጦች እየመጡ መሆኑን መገንዘብ መቻላቸውን አንስተው፥ አነዚህ ለውጦች ተጠናክረው መቀጠል አለባቸው ማለታቸውን ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

