Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ከንቲባ አዳነች አቤቤ በየካ ክፍለ ከተማ የተቋቋመውን የምገባ ማዕከል መርቀው ከፈቱ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 11፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ በየካ ክፍለ ከተማ በኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ድርጅት የተቋቋመውን የምገባ ማዕከል መርቀው ከፈቱ፡፡
ከንቲባ ወይዘሮ አዳነች አቤቤ በዛሬው እለት የ60 ቀናት እቅድ አካል የሆነውንና በኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ድርጅት በየካ ክፍለ ከተማ የተቋቋመውን የምገባ ማዕከል መርቀው ከፍተዋል።
ማዕከሉ 200 ዜጎች በቀን መመገብ የሚያስችል ነው ተብሏል።

ከንቲባ አዳነች በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ባደረጉት ንግግር እንደገለጹት፥ መጀመሪያ ለሰው የሚሆን ነገር ሳይሰራ አገር እቀይራለሁ ማለት አይቻልም፡፡

“እናንተ በቀን አንድ ጊዜ ለመመገብ በምትቸገሩበት አካባቢ እኛ በቀን ሶስት ጊዜ እየበላን መቀጠል የለብንም” ያሉት ከንቲባ አዳነች÷ “የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ስራዎች ኮርፖሬሽን የምገባ ማዕከሉን በመክፈቱ ምስጋና አቅርበዋል፡፡

ኢትዮጵያ የምትቀየረው ሁሉም ሲተባበር እና ኃላፊነቱን ሲወጣ ነው ያሉት ከንቲባዋ÷ ዜጎች በየአካባቢያቸው ወገኖቻቸውን እንዲያስቡም ጠይቀዋል፡፡

በመዲናዋ ያሉ በርካታ ተቋማት የከተማውን ህዝብ ጫና ማቃለል እንዳለባቸው ጠቁመው÷ ለዚህም ሁሉም መስሪያ ቤቶች ከኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ድርጅት መማር አለባቸው ብለዋል፡፡

የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ድርጅት ከዚህ በፊት የምገባ ማዕከላት ስራ ሲጀመር አንዱን ማዕከል በነፃ በመገንባት አስተዋፅኦ ማበርከቱን ገልጸው፥ ዛሬ የተመረቀው የምገባ ማዕከል ቋሚ ወጪ ከኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሰራተኞችና ኃላፊዎች የወር ደመወዝ መዋጮ የሚቀጥል ይሆናል መባሉን የከንቲባ ጽሕፈት ቤት መረጃ ያመላክታል፡፡

ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
Exit mobile version