አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 23፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የሰው ልጅ ለምስጋና ምክንያት ሊያጣ አይችልም ሲሉ የሰባተኛ ቀን አድቬንቲስት ቤተክርስቲያን አማኞች ተናገሩ፡፡
የኢትዮጵያ ሰባተኛ ቀን አድቬንቲስት ቤተክርስቲያን የምስጋና መርሐ ግብር ተካሂዷል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይ ዝማሬና የተለያዩ አገልግሎቶች ተከናውነዋል፡፡
የሃይማኖቱ ተከታዮች እንደገለጹት÷ ምስጋና ብርሃንና ጨለማን ስላፈራረቀ፣ ሕይወትን ስለሰጠና የመንገድ ሁሉ መሪ ለሆነው ፈጣሪ የሚቀርብ ከእምነት መሠረቶች መሀል ቀዳሚው ነው፡፡
በመንገዳችን ሁሉ የምስጋናን አስፈላጊነት ማወቃቸውን ገልጸው÷ ይህ አወንታዊ ሀሳብን የሚያዳብረው ልምምድ በትውልዱ ላይና በሀገር ላይ ሊጋባ ይገባል ብለዋል፡፡
ለሀገር የሠሩ ምስጋናና እውቅና እንደሚገባቸው የጠቆሙት አማኞቹ÷ ምስጋና አወንታዊ ሀሳቦችን በማባዛት ትልቅ ሚና እንዳለው ገልጸዋል፡፡
ሁሉም ይሄንን አወንታዊ ባህል መለማመድ እንዳለበትም አመላክተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ታመስግን አካል የሆነው የምስጋና መርሐ ግብር በኢትዮጵያ ሰባተኛ ቀን አድቬንቲስት አጥቢያዎች ሁሉ መካሄዱን የቤተክርስቲያኗ መረጃ ያመለክታል፡፡
በአፈወርቅ እያዩና አዲሱ ሙሉነህ
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

