አዲስ አበባ ፣ ሐምሌ 29 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል እና የኦሮሚያ ክልል ሕዝቦችን አብሮነት ለማጠናከር ያለመ የምክክር መድረክ በአሶሳ ከተማ ዛሬ መካሄድ ጀምሯል።
የኦሮሚያ፣ የቤኒሻንጉል እና የጋምቤላ ክልሎች የሠላምና ልማት ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤት የተዘጋጀው መድረኩ የሁለቱን ክልሎች አብሮነት ለማጠናከር ያለመ ነው።
በመድረኩም የሁለቱ ክልሎች ከፍተኛ አመራሮች እንዲሁም የማስተባበሪያ ጽህፈት ቤቱ፣ የተጎራባች ወረዳዎች አመራሮች እና የማኅበረሰብ ተወካዮች ተገኝተዋል።
ማስተባበሪያ ጽህፈት ቤቱ ከተቋቋመ ወዲህ በሠላም ግንባታ፣ የተፈናቀሉ ዜጎችን በመደገፍና በመልሶ ማቋቋም፣ በተቋማት ግንባታ፣ በሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነት በርካታ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ተገልጿል።
በመድረኩም የሁለቱን ሕዝቦች አብሮነት በማይፈልጉ ኃይሎች የሚፈጠሩ ችግሮችን በመታገል ለሕዝቦቹ ሠላምና ልማት በጋራ መስራት በሚያስችሉ ጉዳዮች ዙሪያ ውይይት እየተካሄደ መሆኑን የቤኒሻንጉል ክልል ኮሙኒኬሽን መረጃ ያመላክታል።
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

