Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

የደቡብ ክልል ለመከላከያ ሠራዊት ከ219 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት ድጋፍ አደረገ

አዲስ አበባ ፣ ጳጉሜን 4 ፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) የደቡብ ክልል ለሀገር መከላከያ ሠራዊት 219 ነጥብ 1ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት የአይነት ድጋፍ አድርጓል።

የደቡብ ክልል የድጋፍ አሰባሳቢ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ስንታየሁ ወልደሚካኤል÷ አሸባሪው ህወሓት በሀገሪቱ የከፈተውን ጦርነት ለመመከት የህይወት መስዋዕትነት እየከፈለ ላለው ለጀግናው የሀገር መከላከያ ሰራዊት የክልሉ ህዝብ እና መንግስት ለ6ኛ ዙር 219 ሚሊየን 102 ሺህ 686 ብር የሚያወጣ የአይነት ድጋፍ ማድረጉን ተናግረዋል፡፡

ድጋፉ 1 ሺህ 829 ሰንጋዎች፣ 4 ሺህ 520 በግና ፍየል እንዲሁም ግምታዊ ዋጋው ከ65 ነጥብ 9 ሚሊየን በላይ ብር የሚያወጣ ዱቄት፣ በሶ፣ ስኳር፣ የምግብ ዘይት እና መሰል የምግብ አይነቶችን ያካተተ መሆኑ ተገልጿል፡፡

ድጋፉን የተረከቡት የመከላከያ ሚኒስትር ዴኤታ ማርታ ሉዊጂ በበኩላቸው÷የኢትዮጵያ ህዝብ በሁሉም ግንባር ተሰልፎ ለሀገር መከላከያ ሰራዊት ደጀንነቱን እያሳየ መሆኑን ተናግረዋል።

የደቡብ ክልል ህዝብ የጠላትን ወረራ ለማክሸፍ እንዲሁም ሰራዊቱ አዲስ ዓመትን በደስታ እንዲያሳልፍ ላደረገው የላቀ ድጋፍ ምስጋና ማቅረባቸውን ከክልሉ ኮሙኒኬሽን ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡

ጀግኖች ልጆቻችን ምንም የስንቅ ድጋፍ ሳይጎድልባቸው የሀገርን ሉዓላዊነት ለማስከበር እየታገለ ላለው ሰራዊት የክልሉ ህዝብና መንግስት ከፍተኛ ድጋፍ እያደረገ በመሆኑ ምስጋና አቅርበዋል።

Exit mobile version