አዲስ አበባ፣ ሰኔ 23፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) አሜሪካ በኢትዮጵያ ላይ ጥላው የነበረውን የሰብዓዊ መብት ጥስት ክስ በማንሳት ሀገሪቱ ከዚህ በኋላ ምንም አይነት የፋይናንስ ድጋፍና አቅርቦት ክልከላ እንደማይደረግባት አስታወቀች።
የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤት ሰነድን ዋቢ አድርጎ ፎሬይን ፖሊሲ መፅሄት እንደፃፈው፥ ዋሽንግተን በኢትዮጵያ ላይ የምታነሳውን የሰብዓዊ መብት ጥስት ክስን ጥላለች።
ለሀገሪቱ ኮንግረስ የተላከው ይህ የውስጥ ማስታወሻ አሜሪካ ይህንን ክስ በማንሳቷ ከዚህ በኋላ የውጭ ጉዳይ መሥሪያ ቤቱ ኢትዮጵያ ከዋሽንግተንም ሆነ ከሌሎች ዓለም አቀፍ አበዳሪዎች ገንዘብ እንዳታገኝ ሲያደርግ የነበረውን መከላከል ያቆማል ይላል።
የአሜሪካ ውሳኔ ኢትዮጵያ ከዓለም አቀፉ የገንዘብ ተቋም (አይ ኤም ኤፍ) እና ከዓለም ባንክ የገንዘብ ድጋፍና ብድር እንድታገኝ የሚያስችል ነው።
ውሳኔው፥ ዋሽንግተን በሰሜኑ ጦርነት ወቅት የሻከረውን የሁለቱን ሀገራት ግንኙነት ለማደስ ፍላጎት እንዳላት ያሳያል ብሏል መፅሔቱ።