Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

በጎነትን በዕለተ ተዕለት እየተገበርነው ልንኖረው የሚገባን ጉዳይ ነው – አቶ ብናልፍ አንዷለም

አዲስ አበባ፣ ጳጉሜን 3፣ 2015 (ኤፍ ቢ ሲ) በጎነትን በዕለተ ተዕለት ኑሯችን ውስጥ እየተገበርነው ልንኖረው የሚገባን ጉዳይ ነው ሲሉ የሰላም ሚኒስትር ብናልፍ አንዷለም ተናገሩ።

የበጎነት ቀን ‘በጎነት ለሀገር’ በሚል መሪ ሃሳብ በተለያዩ መርሐ ግብሮች በሀገር አቀፍ ደረጃ እየተከበረ ይገኛል።

የበጎነት ቀንን አስመልክቶ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ከሰላም ሚኒስቴርና ከሌሎች ተቋማት ጋር በመተባበር በጎነት ለሀገር በሚል ሃሳብ ከባለድርሻ አካላት ጋር የፓናል ውይይት አካሂዷል።

የሰላም ሚኒስትር ብናልፍ አንዷለም በዚሁ ጊዜ÷ እንደ ሀገር በሚደረገው የለውጥ ጉዞ ውስጥ በጎነት የራሱ ትልቅ ድርሻ እንዳለው ገልጸው በጎነትን በዕለተ ተዕለት ኑሯችን ውስጥ መተግባር ይገባል ብለዋል፡፡

የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ኤርጎጌ ተስፋዬ (ዶ/ር) በበኩላቸው÷ በጎነት ያለ ምንም ክፍያ ሀገርንና ሕዝብን በማገልገል የሚገኝ ትልቅ አቅም ነው ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡

ከቅርብ ዓመታት ወዲህ ወጣቶች በተደራጀ መልኩ በሀገር አቀፍ ደረጃ በስፋት እየተሳተፉበት ያለው የበጎ አድራጎት ስራ ትልቅ ውጤት እያስመዘገበ መሆኑን በመጥቀስም ባህል ሆኖ እንዲቀጥል ሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ እየሰራ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

የመቄዶንያ የአረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል መስራች ቢንያም በለጠ በመድረኩ ተገኝተው ባስተላለፉት መልዕክት ÷በጎ ተግባር መስዋዕትነት ጭምር የሚጠይቅ እና ለሌሎች የመኖር ድርሻ መሆኑን አንስተዋል።

Exit mobile version