አዲስ አበባ፣ መስከረም 24፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የኢሬቻ በዓል በሰላም እሴቱን ጠብቆ እንዲከበር አስፈላጊው ዝግጅት መደረጉን የኦሮሚያ ክልል የመንግሥት ኮሙዩኒኬሽን ቢሮ አስታውቋል፡፡
የቢሮ ሃላፊው አቶ ሃይሉ አዱኛ በሰጡት መግለጫ÷ ኢሬቻ የኦሮሞ ሕዝብ ክረምቱ በሰላም በመጠናቀቁ ሁሉን ነገር ለፈጠረ አምላክ ምስጋና የሚያቀርብበትና መጪው ዘመን መልካም እንዲሆን ፈጣሪን የሚለምንበት በዓል ነው ብለዋል፡፡
ኢሬቻ የምስጋና፣ የአንድነት፣ የወንድማማችነት፣ የይቅርታና የብሩህ ተስፋ በዓል እንደሆነም አስገንዝበዋል።
በዓሉ በሰላም እሴቱን ጠብቆ እንዲከበርም ከሚመለከታቸው አካላት ጋር አስፈላጊው ዝግጅት መደረጉን ነው የገለጹት፡፡
በአዲስ አበባ እና በቢሾፍቱ የሚከበረው የኢሬቻ በዓል አባገዳዎች ባስቀመጡት አቅጣጫ መሰረት መከናወን እንዳለበት መናገራቸውንም የክልሉ ኮሙኒኬሽን መረጃ ያመላክታል፡፡
የበዓሉ ታዳሚዎች በዓሉን የማይገልጹ አርማዎችን መያዝ እንደሌለባቸው አሳስበዋል፡፡