አዲስ አበባ፣ መስከረም 28፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያ በጃፓን ኪዮቶ እየተካሄደ ባለው 18ኛው የበይነ-መረብ አስተዳደር ጉባኤ ላይ እየተሳተፈች ነው።
“ለምንፈልገው በይነ-መረብ ግንኙነት ሁሉንም ሰዎች ማብቃት” በሚል መሪ ሃሳብ እየተካሄደ ያለው ጉባኤ በተለያዩ ጉዳዮች ዙሪያ እየመከረ ነው።
ሰው ሰራሽ አስተውህሎትና አዲሱ ቴክኖሎጂ፣ የበይነ-መረብ ክፍፍልን ማስቀረት፣ የመረጃ መረብ ደህንነት፣ የመረጃ መረብ ወንጀልና የኦንላይን ደህንነት፣ የዳታ አስተዳደርና አካታችነት፣ የሰብዓዊ መብትና ነፃነት እንዲሁም ዘላቂነት የሚሉት የጉባኤው አጀንዳዎች ናቸው።
በመድረኩ ላይ የዓለም አቀፉ የበይነ-መረብ አስተዳደር ጉባኤ የከፍተኛ መሪዎች አባልና ኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዴኤታ ሁሪያ አሊ እየተሳተፉ ነው።
ሚኒስትር ዴኤታዋ በበይነ-መረብ አስተዳደር ዙሪያ የታዳጊ ሀገራትን ፍላጎቶች ያነሳሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ከኢኖቬሽንና ቴክኖሎጂ ሚኒስቴር ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡
17ኛውን የበይነ-መረብ አስተዳደር ጉበኤን ባለፈው ዓመት ኢትዮጵያ ማዘጋጀቷ አይዘነጋም፡፡