Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ኢትዮጵያ የዓለም አቀፉን የስደተኞች መርህ በመከተል ለስደተኞች ድጋፍ እያደረገች ነው ተባለ

አዲስ አበባ፣ ታኅሣስ 4፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ኢትዮጵያ የዓለም አቀፉን የስደተኞች መርህ በተከተለ መንገድ ለስደተኞች ሁሉን አቀፍ ድጋፍ እያደረገች መሆኑን የገንዘብ ሚኒስትር ዴኤታ ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) ገለጹ።

ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር)÷ ከሁለተኛው የዓለም አቀፍ የስደተኞች ፎረም ጎን ለጎን ከኔዘርላንድስ የውጭ ንግድና ልማት ትብብር ምክትል ሚኒስትር ፓስካል ግሮተንሁይስ እና የዴንማርክ የልማት ፖሊሲ ዋና ፀሃፊ ሎተ ማቾን ጋር ውይይት አካሂደዋል፡፡

በውይይታቸውም÷ ኢትዮጵያ የዓለም አቀፉን የስደተኞች መርህ ተከትላ ሁሉን አቀፍ ድጋፍ ለስደተኞች ማድረጓን ኢዮብ ተካልኝ (ዶ/ር) አንስተዋል፡፡

ኢትዮጵያ ስለተገበረችው የኢኮኖሚ ማሻሻያ እና ስላስመዘገበችው ውጤት እንዲሁም የጋራ ብልጽግናን ማረጋገጥ ስለሚቻልበት ሁኔታም ገለጻ አድርገዋል።

በኢትዮጵያና በሁለቱ ሀገራት መካከል ያለውን የቆየ ትብብር አድንቀው÷ የዓለም አቀፍ የስደተኞች ፎረም ስደተኞች ሰርተው የሚለወጡበትን እድል መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡

የኔዘርላንድስ የውጭ ንግድና ልማት ትብብር ምክትል ሚኒስትር ፓስካል ግሮተንሁይስ እና የዴንማርክ የልማት ፖሊሲ ዋና ፀሃፊ ሎተ ማቾን÷ ኢትዮጵያ ለስደተኞች ዓለም አቀፍ ጥበቃና መፍትሄ በመስጠት ያላትን የመሪነት ሚና አድንቀዋል።

ከኢትዮጵያ ጋር በስደተኞች ጉዳይ ላይ በሁለትዮሽ እና በባለብዙ ወገን ትብብር በጋር ለመስራት ያላቸውን ቁርጠኝነትም እንደገለጹ ኢዜአ ዘግቧል፡፡

Exit mobile version