አዲስ አበባ፣ ታኅሣስ 8፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) የመከላከያ ሰራዊት ፋውንዴሽን የሚያመርታቸው የግብርና ልማት ውጤቶች፣ ወታደራዊ መለዮ ልብስ፣ የማዕረግ ምልክቶች ማምረቻና ሌሎች ተግባራትን የሚያሳይ የፎቶ ዐውደ-ርዕይ ተከፍቷል፡፡
ዐውደ-ርዕዩን የከፈቱት÷ የመከላከያ ሚኒስትር አብርሃም በላይ (ዶ/ር)፣ የግብርና ሚኒስትር ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) እና የመከላከያ ሠራዊት ፋውንዴሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ብርጋዲየር ጄኔራል ደረጄ መገርሳ ናቸው፡፡
በዐውደ-ርዕዩ የተቀናጀ የግብርና ልማት፣ የሜዳሊያ፣ ባጅ፣ ሬንጀር እና የመኝታ ከረጢት ማምረቻ እንዲሁም የማዕረግ መስሪያ እና ሌሎች የመከላከያ ፋውንዴሽን የምርት ውጤቶች ለዕይታ ቀርበዋል።
ሠራዊቱን በትጥቅና በቴክኖሎጂ ከማደራጀት ባለፈ የምግብ ፍጆታውን በራስ ዐቅም ለመሸፈን እየተሠራ መሆኑን አብርሃም በላይ (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡
ለዚህም በተለያዩ የግብርና ልማት ሥራዎች ላይ ትኩረት ተደርጓል ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል፡፡
ሠራዊቱ ኅብረተሰቡን በግብርና ሥራዎች በማገዝ የሕዝብ አለኝታነቱን እያስቀጠለ እንደሚገኝ ጠቁመው÷ የራሱን የምግብ ፍጆታ ለማሟላትም በሚያከናውነው ተግባር ተጨባጭ ውጤት እየመጣ ነው ብለዋል፡፡
ከዐውደ-ርዕዩ ጎን ለጎን÷ የመከላከያ ሰራዊቱ የ2015/16 ዓ.ም የመኸር ሰብል ልማት አፈፃጸም ሪፖርት፣ የቀጣይ 2016/17 ዓ.ም ዕቅድ እና የሰባት ዓመታት የግብርና ልማት ስትራቴጂክ ዕቅድ ምክክር እየተካሄደ ይገኛል።
የሀገርን ሰላምና ደኅንነት ከማስጠበቅ ጎን ለጎን በግብርና ልማት ሥራዎች የተሻለ አፈፃጸም ያከናወኑ ክፍሎች የሜዳሊያ ሽልማት እንደሚበረከትላቸው ተመላክቷል፡፡
#Ethiopia
ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- https://www.facebook.com/fanabroadcasting
ዩትዩብ፦ https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ትዊተር፦ https://twitter.com/fanatelevision
ኢንስታግራም፦ https://www.instagram.com/fana_television/
ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!