Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

በኦሮሚያ ክልል ከግማሽ ሚሊየን በላይ ሰዎችን ተጠቃሚ የሚያደርጉ የውኃ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት በቅተዋል

አዲስ አበባ፣ ታኅሣስ 24፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በኦሮሚያ ክልል በተጠናቀቀው ግማሽ ዓመት ከ500 ሺህ በላይ ወገኖችን መድረስ የቻሉ 2 ሺህ 618 የውኃ ፕሮጀክቶች ለአገልግሎት ክፍት መደረጋቸውን የክልሉ ውኃና ኢነርጂ ቢሮ አስታወቀ፡፡

የቢሮው ምክትል ኃላፊ መሐመድ ኑራ (ኢ/ር) ለፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንዳሉት÷ በግማሽ ዓመቱ ለአገልግሎት ክፍት ለተደረጉት እና አሁንም ግንባታቸው ወደ መጠናቀቁ ለተቃረቡ የውኃ ፕሮጀክቶች 4 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ወጪ ተደርጓል፡፡

ወጪውም÷ በክልሉ መንግሥት፣ መንግሥታዊ ባልሆኑ ድርጅቶች፣ በሕብረተሰብ ተሳትፎ እና በፕሮግራሞች (ከተለያዩ የልማት አጋሮች በተገኘ ድጋፍ) መሸፈኑን አብራርተዋል፡፡

በአጠቃላይ በ2016 በጀት ዓመት 11 ነጥብ 3 ቢሊየን ብር ተመድቦ ከ10 ሺህ በላይ የውኃ ፕሮጀክቶችን ለመገንባት ዕቅድ ተይዞ እየተሠራ መሆኑን ጠቁመዋል።

ከ11 ነጥብ 3 ቢሊየኑ ብር 7 ነጥብ 6 ቢሊየኑ በክልሉ መንግስት እንደሚሸፈንም ነው ያረጋገጡት፡፡

ባለፉት ሥድስት ወራት ያልተጠናቀቁትን ጨምሮ ሌሎች ፕሮጀክቶችን በበጀት ዓመቱ ለማጠናቀቅ እየሠሩ መሆናቸውንም ጠቅሰዋል፡፡

በዮሐንስ ደርበው

ወቅታዊ፣ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
ድረ ገጽ፦ https://www.fanabc.com/
ፌስቡክ፡- FBC(Fana Broadcasting Corporate S.C.)
ቴሌግራም፦ https://t.me/fanatelevision
ቲክቶክ፦ https://www.tiktok.com/@fana_television በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!
Exit mobile version