አዲስ አበባ፣ ግንቦት 16፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ከ4 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል በላይ የአፈር ማዳበሪያ ወደ አማራ ክልል መግባቱን የክልሉ ግብርና ቢሮ አስታወቀ፡፡
ለ2016/17 የምርት ዘመን ለክልሉ የሚያስፈልገው 8 ሚሊየን 57 ሺህ 900 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ግዥ መፈጸሙንም ነው ቢሮው የገለጸው፡፡
ግዥ ከተፈፀመው ማዳበሪያ መካከልም እስከ አሁን ከ5 ነጥብ 3 ሚሊየን ኩንታል በላይ ወደብ መድረሱን ያመላከተው ቢሮው÷ ከዚህ ውስጥም ከ4 ነጥብ 5 ሚሊየን ኩንታል የሚልቀው ወደ ክልሉ ገብቷል ብሏል፡፡
እንዲሁም 3 ሚሊየን 936 ሺህ 397 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ከዩኒየኖች መጋዝን ወደ ኅብረት ሥራ ማኅበራት ተጓጉዟል መባሉን የቢሮው መረጃ አመላክቷል፡፡
በሌላ በኩል 3 ሚሊየን 547 ሺህ 347 ኩንታል የአፈር ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ መሠራጨቱ ተጠቅሷል፡፡
በክልሉ በምርት ዘመኑ 5 ነጥብ 1 ሚሊየን ሄክታር መሬት በዘር በመሸፈን 169 ሚሊየን ኩንታል ለማምረት ታቅዶ እየተሰራ መሆኑም ተገልጿል፡፡