አዲስ አበባ፣ ሐምሌ 5፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) በቀጣዮቹ አስር ቀናት የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የሀገሪቱ አንዳንድ አካባቢዎች ከባድ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚጠበቅ የኢትዮጵያ ሜቲዎሮሎጂ ኢንስቲትዩት አስታውቋል፡
ኢንስቲትዩቱ በሚቀጥሉት አስር ቀናት የክረምት ዝናብ ተጠቃሚ በሆኑ የሀገሪቱ አካባቢዎች የዝናብ ስርጭቱ እየተጠናከረ እንደሚሔድ ገልጿል፡፡
የሚጠበቀው እርጥበት የመካከለኛ ጊዜ ሰብሎችን ለመዝራት ፣በተለያየ የእድገት ደረጃ ላይ ለሚገኙ የመኸር ሰብሎች የውሃ ፍላጎትን ለማሟላት እንደሚረዳ የትንበያ መረጃዎች አመልክተዋል፡፡
በዚሁ ወቅት በደቡብ ምዕራብ፣ በምዕራብ፣ በሰሜን ምዕራብ፣ በሰሜን፣ በመካከለኛው እና በሰሜን ምስራቅ የሀገሪቱ ስፍራዎች በ24 ሰዓት ውስጥ ከ 30 ሚሊ ሜትር በላይ ከባድ ዝናብ እንደሚጠበቅም ተጠቁሟል።
በኦሮሚያ፣ አማራ፣ አዲስ አበባ፣ ሐረር፣ ድሬዳዋ፣ አፋር፣ ቤንሻንጉል፣ ማዕከላዊ ኢትዮጵያ፣ ደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ እና ደቡብ ኢትዮጵያ ክልሎች በብዙ ቦታዎቻቸው ላይ ከቀላል እስከ መካከለኛ መጠን ያለው ዝናብ እንደሚጠበቅ ተጠቅሷል፡፡
በዚሁ የክረምት ወቅት የሚኖረው እርጥበት የሰብሎችን የውሃ ፍላጎት ለማሟላት፣ የግብርና ተግባራትን ለማከናወን፣ ለመጠጥ ውሃ አቅርቦትና ለግጦሽ ሳር ልምላሜም አዎንታዊ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ነው የተገለጸው።
እንዲሁም በተፋሰሶች ያለውን የገጸ ምድርና የከርሰ ምድር የውሃ ሃብትን ከማሻሻል እና የግድቦችንና የወንዞችን የውሃ መጠን ከማሳደግ አንጻር አዎንታዊ ሚና እንደሚኖረው ተጠቅሷል፡፡
በሌላ በኩል በአንዳንድ አካባቢዎች ላይ የሚኖረው ከባድ ዝናብ በማሳዎች ላይ የውሃ መተኛት፣ የአረም መስፋፋት ሊያስከትል እንደሚችል መነገሩን የኢንስቲትዩቱ መረጃ ያመላክታል ።
በተጨማሪም ከእርጥበት ጋር የተያያዙ የሰብል በሽታዎች ሊከሰቱ ስለሚችሉ ቅድመ ዝግጀት ማድረግ እንደሚገባ ተጠቁሟል፡፡
የሚኖረው ዝናብ ከሚኖረው ጠቀሜታ ባሻገር ጎርፍ ሊያስከትል ስለሚችል ህብረተሰቡ ጥንቃቄ እንዲያደርግም ኢንስቲትዩቱ አሳስቧል፡፡