Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ከሰኔ 24 ጀምሮ በተለያዩ ከተሞች በሚገኙ ባንኮች የፋይዳ መታወቂያ እንደ ቅድመ ሁኔታ ይተገበራል

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 21፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ከሰኔ 24 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በ25 የክልል ከተሞች በሚገኙ ባንኮች አዲስ የባንክ አካውንት ለመክፈት የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ ይዞ መቅረብ እንደ ቅድመ ሁኔታ ተግባራዊ ይደረጋል አለ የኢትዮጵያ ብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም፡፡

የብሔራዊ መታወቂያ ፕሮግራም የስትራቲጂክ ኮሙኒኬሽን ዳይሬክተር አቤኔዘር ፈለቀ ለፋና ዲጂታል እንዳሉት÷ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ ባወጣው መመሪያ መሰረት ነው ቅድመ ሁኔታው የሚተገበረው።

በዚህም ከታሕሣሥ 23 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በአዲስ አበባ በሚገኙ በሁሉም ባንኮች አዲስ የባንክ ሒሳብ ለመክፈት የፋይዳ ዲጂታል መታወቂያ እንደ ቅድመ ሁኔታ ተግባራዊ ተደርጎ እየተተገበረ መሆኑን አስታውሰዋል።

በተመሳሳይም ከሰኔ 24 ቀን 2017 ዓ.ም ጀምሮ በባህር ዳር፣ ደሴ፣ ጎንደር፣ ደብረ ብርሃን፣ ኮምቦልቻ፣ ሸገር፣ አዳማ፣ ሻሸመኔ፣ ቢሾፍቱ፣ ጅማ፣ ባቱ፣ ሆሳዕና፣ አምቦ፣ ወልቂጤ እና ሐዋሳ ከተሞች አዲስ የባንክ ደብተር ለመክፈት እንደ መጀመሪያ ቅድመ ሁኔታ ተግባራዊ ይደረጋል ብለዋል።

በተጨማሪም በሀረር፣ ወላይታ ሶዶ፣ መቀሌ፣ ወራቤ፣ አዲግራት፣ ድሬዳዋ፣ አርባምንጭ፣ ጅግጅጋ፣ አክሱም እና ቡታጅራ ከተሞች ተግባራዊ እንደሚሆንና ይህም ሥራ እየሰፋ እንደሚሄድ ጠቁመዋል።

ለዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ከ3 ሺህ በላይ የምዝገባ መሳሪያዎች ተገዝተው አገልግሎት ላይ እየዋሉ መሆኑንና ከ1 ሺህ በላይ ምዝገባ ጣቢያዎች በሀገር አቀፍ ደረጃ አገልግሎት እየሰጡ እንደሆነም አብራርተዋል።

እስካሁን ከ18 ሚሊየን በላይ ዜጎች የዲጂታል መታወቂያ ምዝገባ ማካሄዳቸውን አንስተው÷ ሁሉም ዜጋ ምዝገባውን እንዲያካሂድ ከባለድርሻ አካላት ጋር በመተባበር ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ እየተሰራ ነው ብለዋል።

የፋይዳ መታወቂያን ከተለያዩ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ጋር የማስተሳሰር ሥራ እየተሰራ እንደሆነ ጠቁመው÷ እስካሁን ከ55 ተቋማት ጋር ማስተሳሰር ተችሏል ነው ያሉት።

በአድማሱ አራጋው

ፈጣን እና ወቅታዊ መረጃዎችን ለማግኘት፡-

YouTube www.youtube.com/@fanamediacorporation
Facebook www.facebook.com/fanabroadcasting
Telegram t.me/fanatelevision
Website www.fanamc.com
TikTok www.tiktok.com/@fana_television
WhatsApp www.whatsapp.com/channel/0029VbB0dRxG8l59MUkoWR29
Amharic Entertainment YouTube www.youtube.com/@fanaentertainment
Facebook www.facebook.com/wmccwaltamediaandcommunicationcorporate
TikTok www.tiktok.com/@fanamc_entertainment
Amharic Documentary YouTube www.youtube.com/@fanamcdocumentary በመወዳጀት ይከታተሉን፡፡
ዘወትር፦ ከእኛ ጋር ስለሆኑ እናመሰግናለን!

Exit mobile version