አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 1፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ሰብሳቢ ወ/ሮ ሜላትወርቅ ኃይሉ የምርጫ ሂደትን በተመለከተ ግንዛቤ የመፍጠር ስራ እየተሰራ ነው አሉ።
ወ/ሮ ሜላትወርቅ ኃይሉ ከፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ጋር በነበራቸው ቆይታ፤ ቀጣዩን ሀገራዊ ምርጫ በተያዘለት የጊዜ ሰሌዳ መሰረት ለማካሄድ ዝግጁ ነን ብለዋል።
ቦርዱ በ2011 ዓ.ም በአዲስ መንገድ ከተደራጀ በኋላ አንድ ሀገራዊ ምርጫ እና ሶስት ህዝበ ውሳኔ አካሂዷል ሲሉ አስታውሰዋል።
ይህ ሂደት በተቋሙ ላይ የፈጠረው አቅም ቦርዱ መስራት የሚችልበት ምቹ ሁኔታ መፍጠሩን ተናግረዋል።
የቦርዱ አባላትን ጨምሮ የተቋሙን የሰው ሃይል አቅም የማጠናከር እና ወደ 20 ሺህ የምርጫ ጣቢያዎችን በጂአይኤስ የማስተሳሰር ስራ መሰራቱን ገልጸዋል።
በዚህም የምርጫ ታዛቢዎች ምርጫ ጣቢያዎችን በቀላሉ ማግኘት የሚችሉበትን ያካተተ መረጃ ሰብስበናል ነው ያሉት።
የምርጫ ቁሳቁሶች ስርጭት በሚከናወንበት ወቅት ምን ሊያጋጥም እንደሚችል የተነተነ የመረጃ ዝግጅት እንዳለ ገልጸው፤ ቦርዱ ቀጣዩን ሀገራዊ ምርጫ ለማካሄድ የሚያስችል ቁመና ላይ እንደሚገኝ አስታውቀዋል።
የምርጫ ሂደትን በተመለከተ ትምህርት ቤቶችን ጨምሮ በተለያዩ አካባቢዎች ግንዛቤ የመፍጠር ስራ እየተሰራ ነው ብለዋል።
ተደራሽነታቸው ውስን በሆኑ አካባቢዎች የማህበረሰብ ሬዲዮ አማራጭን በመጠቀም ግንዛቤ የማስጨበጥ ተግባር እየተከናወነ እንደሆነ አመልክተዋል።
ቦርዱ በራሱ ከሚሰራው የግንዛቤ ማስጨበጥ ተግባር በተጨማሪ ከሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ጋር በመተባበር እየሰራ እንደሆነም ጠቁመዋል።
በዮናስ ጌትነት