Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ፕሬዚዳንት ፑቲን የዩክሬኑ አቻቸው ሞስኮን እንዲጎበኙ ጋበዙ

አዲስ አበባ፣ ነሐሴ 28፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) የሩሲያ ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን የዩክሬኑ አቻቸው ቮሎድሚር ዘለንስኪ በሩሲያ ሞስኮ ጉብኝት እንዲያደርጉ እና ከእርሳቸው ጋር እንዲወያዩ ጋበዙ፡፡

ፕሬዚዳንት ፑቲን የቻይና ጉብኝታቸውን አስመልክተው መግለጫ ሰጥተዋል፡፡

በመግለጫቸውም በቻይና የነበራቸው ጉብኝት ፍሬያማ እንደነበር እና ጉብኝቱ የሩሲያ እና የቻይናን የወደፊት ትብብር ሚያጠናክር መሆኑን ገልፀዋል፡፡

በጉብኝቱ ዩክሬንን ጨምሮ ማንኛውም ሀገር ብሔራዊ ደህንነቱን ማስጠበቅ እንደሚችል ነገር ግን ማንኛውም ሀገር የብሔራዊ ደህንነቱን በሩሲያ ኪሳራ ላይ ሊያወራርድ እንደማይገባ ከመሪዎች ጋር በነበራቸው ውይይት ማንሳታቸውን ተናግረዋል።

የዩክሬኑ ፕሬዚዳንት ቮሎድሚር ዘለንስኪ በጦርነቱ ዙሪያ ለመምከር ከፈለጉ ሞስኮ በሯ ክፍት እንደሆነ አረጋግጠዋል።

የዘለንስኪ የስልጣን ጊዜ ከማብቃቱ በፊት ትርጉም ያለው ውይይት ማድረግ እንደሚችሉ ፍንጭ መስጠታቸውን ቢቢሲ እና ስፑትኒክ ኒውስ ዘግበዋል፡፡

 

በሚኪያስ አየለ

Exit mobile version