Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

በአፍሪካ ግዙፉ የአሊኮ ዳንጎቴ የነዳጅ ማጣሪያ ፋብሪካ…

አዲስ አበባ፣ መስከረም 6፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የናይጀሪያዊው ባለሀብት አሊኮ ዳንጎቴ የነዳጅ ማጣሪያ ፋብሪካ በ60 ቀናት ውስጥ 1 ነጥብ 1 ቢሊየን ሊትር ነዳጅ ለገበያ አቅርቧል፡፡

የነዳጅ ማጣሪያ ፋብሪካው ስራ የጀመረበት አንደኛ ዓመት አከባበር ላይ ባለሀብቱ አሊኮ ዳንጎቴ÷ ፋብሪካው ከሰኔ እስከ መስከረም ወር መጀመሪያ ድረስ ብቻ 1 ነጥብ 1 ቢሊየን ሊትር ነዳጅ ለሀገር ውስጥ እና የውጭ ገበያ ማቅረቡን ተናግረዋል፡፡

ፋብሪካው የናይጀሪያን የነዳጅ ፍላጎት ሙሉ በሙሉ የመሸፈን አቅም እንዳለው ገልጸው÷ በዓለም የነዳጅ ግብይት ውስጥ በመግባት ለሀገሪቱ የውጭ ምንዛሪ እያስገኘ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡

በአኅጉሪቷ ሁለት የአፍሪካ ሀገራት ብቻ ነዳጅ እንዳማያስገቡ በመጥቀስ ሌሎቹ የአፍሪካ ሀገራት ነዳጅ ከውጭ በማስገባት ለከፍተኛ ወጪ እንደሚዳረጉም ጠቁመዋል፡፡

ፋብሪካው በአኅጉሪቱ ያለውን የነዳጅ ችግር ለመቅረፍ እየሰራ መሆኑን ያመላከቱት አሊኮ ዳንጎቴ÷ አፍሪካውያን የውስጥ ኢንዱስትሪዎችን እንዲያበረታቱ ማስገንዘባቸውን ቢዚነስ ፖስት ናይጄሪያ ዘግቧል።

በሚኪያስ አየለ

Exit mobile version