በደብረ ብርሃን ከተማ 52 ሚሊየን ብር በላይ በሆነ ወጪ ሰብዓዊ እርዳታ ለሚሹ 10 ሺህ 980 ዜጎች የምግብ እና የተለያዩ ቁሳቁስ ድጋፍ ተደርጓል፡፡
ድጋፉን ያደረገው የኢትዮጵያ አዲስ ኪዳን መጥምቃዊት ቤተክርስቲያን ልማት ኮሚሽን መሆኑ ተገልጿል፡፡
የምግብና ቁሳቁስ ድጋፉን የልማት ኮሚሽኑ ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ማሞ ቀጸላም ለከተማዋ ምክትል ከንቲባ ወርቃለማሁ ኮስትሬ አስረክበዋል፡፡
ከተደረገው ድጋፍ ውስጥ 16 ሺህ 470 ሊትር ዘይት፣3 ሺህ 294 ኩታል ጤፍ ፣ 330 ኩንታል አተር፣ 348 ኩንታል አልሚ ምግብ (ፋፋ) እና ሌሎች ቁሳቁስ ይገኙበታል፡፡
አቶ ማሞ ቀጸላም በዚህ ወቅት÷ በከተማዋ ችግር ውስጥ ለሚገኙ ዜጎች የሚደረገው ድጋፍ ተጠናክሮ እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡
ድጋፉ በሁለት ዙር መከናወኑን ጠቁ መው÷ ሁሉም ሕብረተሰብ ድጋፍ ለሚሹ ወገኖች አብሮነቱን ማሳየት እንዳለበት አስገንዝበዋል፡፡
ወርቃለማሁ ኮስትሬ በበኩላቸው የኢትዮጵያ አዲስ ኪዳን መጥምቃዊት ቤተክርስቲያን ልማት ኮሚሽን የሰብዓዊ እርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ዜጎች ላደረገው ድጋፍ ምስጋና አቅርበዋል፡፡
በከተማዋ እርዳታ የሚሹ ዜጎች መኖራቸውን ጠቁመው÷በሰብዓዊ እርዳታ ላይ የተሰማሩ ድርጅቶች ድጋፍ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል፡፡

