Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ኢትዮ ቴሌኮም በግማሽ ዓመቱ ምን ያህል የሞባይል ዳታና የድምጽ ጥሪ አስተናግዷል?

አዲስ አበባ፣ ጥር 21፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ለደንበኞች ጥራቱን የጠበቀ የሞባይል ዳታ እና የድምጽ ጥሪ አገልግሎት ለመስጠት በትኩረት እየተሰራ ነው አሉ የኢትዮ ቴሌኮም ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍሬሕይወት ታምሩ፡፡
ዋና ሥራ አስፈጻሚዋ የተቋሙን የ2018 በጀት ግማሽ ዓመት አፈጻጸም አስመልክተው ለመገናኛ ብዙሃን ባለሙያዎች ማብራሪያ ሰጥተዋል፡፡
በማብራሪያቸውም የሞባይል አገልግሎት ጥራትን ለማሳደግ በተከናወኑ ተግባራት የኔትወርክ መገኘት መጠን 97 ነጥብ 9 በመቶ መድረሱን ተናግረዋል፡፡
ከኔትወርክ ትራፊክ አንጻር በስድስት ወራቱ 92 ነጥብ 38 ቢሊየን ደቂቃ የሞባይል የድምፅ ጥሪ ማስተናገድ መቻሉን አስረድተዋል፡፡
440 ነጥብ 18 ሚሊየን ደቂቃ ወደ ሀገር ውስጥ የተደረገ ዓለምአቀፍ የድምፅ ጥሪ መከናወኑን ጠቁመው÷ 26 ነጥብ 6 ቢሊየን አጭር የጽሑፍ መልዕክት ልውውጥ መደረጉን አመልክተዋል፡፡
እንዲሁም 942 ነጥብ 52 ቢሊየን ሜጋ ባይት የሞባይል ዳታ ትራፊክ መመዝገቡን ነው ፍሬሕይወት ታምሩ የገለጹት፡፡
አፈጻጸሙ ከባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ጋር ሲነጻጸር በድምፅ ጥሪ የ10 ነጥብ 6 በመቶ፣ በሞባይል ዳታ የ46 ነጥብ 8 በመቶ እና ከውጭ ወደ ሀገር ውስጥ የተደረገ ጥሪ በ12 ነጥብ 8 በመቶ ጭማሪ አሳይቷል ብለዋል፡፡
በሁሉም የትራፊክ ዓይነቶች እድገት መመዝገቡን ጠቅሰው ÷ በተለይም የዳታ ትራፊክ አፈጻጸም የላቀ እድገት ማሳየቱን ነው አጽንኦት የሰጡት፡፡
የአፈጻጸም እድገቱም የዳታ ተጠቃሚ ደንበኞች ቁጥርና የዳታ አጠቃቀም ባህሪ መጨመር፣ ተጨማሪ የኔትወርክ መሰረተ ልማቶች (4ጂ ኔትወርክ) መስፋፋትና አዳዲስ ምርትና አገልግሎቶች ወደ ገበያ በመግባታቸው መመዝገቡን ጠቁመዋል፡፡
በሌላ በኩል የኢትዮ ቴሌኮም አገልግሎት ባልደረሰባቸው የገጠር አካባቢዎች የዲጂታል መካተትን ለማረጋገጥና የገጠር ነዋሪዎችን ከዲጂታሉ ዓለም ጋር ለማቀላቀል ሰፊ የማስፋፊያ ሥራዎች እየተከናወኑ መሆኑን ጠቅሰዋል፡፡
ባለፉት 6 ወራት ብቻ በ9 ክልሎችና በ102 ወረዳዎች ውስጥ 130 የገጠር ሞባይል ጣቢያዎችን በመገንባት 332 ቀበሌዎችንና መንደሮችን የቴሌኮም አገልግሎት ተጠቃሚ ማድረግ መቻሉን አመልክተዋል፡፡
በዚህም ከ761 ሺህ በላይ ዜጎች የአገልግሎቱ ተጠቃሚ ሲሆኑ÷ ጣቢያዎቹ የተገነቡባቸው አካባቢዎች በአማካይ ከከተሞች በ23 ነጥብ 76 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኙ መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡
በመላኩ ገድፍ
Exit mobile version