Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ቦርዱ ከሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ጋር ተወያየ

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 11፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ 7ኛውን ጠቅላላ ምርጫ በመታዘብ ላይ ለተሠማሩ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ አካሂዷል፡፡
በመድረኩ የቦርዱ ሰብሳቢ ሜላትወርቅ `ኃይሉ በቅድመ ምርጫ ተግባራት በርካታ ሥራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውን አስታወሰው÷ በምርጫ መታዘብ ሥራ ላይ ለሚሠማሩ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ዕውቅና መስጠት አንዱ ተግባር እንደነበር አንስተዋል፡፡
የታዛቢዎች ተሣትፎ ለምርጫው ግልጽነት፣ አሣታፊነትና ተጠያቂነት ወሣኝ ነው ያሉት ሰብሳቢዋ÷ የመራጮች ምዝገባ ሂደትን ተከትሎ ምርጫውን ለመታዘብ ሪፖርት ላቀረቡ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ምስጋና አቅርበዋል፡፡
የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ምርጫውን ለመታዘብ ሪፖርት ማቅረባቸው ለምርጫ ሥርዓቱ መዘመንና ለዴሞክራሲያዊነቱ ከፍተኛ አስተዋፅዖ እንዳለው አብራርተዋል፡፡
ይህ ትብብር የበለጠ ትርጉም የሚኖረው ሕግን ተከትሎ ሲሠራ መሆኑን በመጥቀስ÷ የዛሬው መድረክም ስለምርጫ የሕግ ማዕቀፍ፣ የታዛቢዎች መመሪያ ምን ይላል ስለሚለውና አጠቃላይ የምርጫ ዑደትን በተመለከተ ግንዛቤ ለማስጨበጥ ያለመ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
መድረኩ ከዚህ በፊት በምርጫ መታዘብ ላይ ተሠማርተው ለሚያውቁ ድርጅቶች የበለጠ ትኩረት አድርገው እንዲታዘቡ እንዲሁም አዲስ ለተመዘገቡት ግንዛቤ ለመስጠት ታስቦ እንደተዘጋጀ መናገራቸውን የቦርዱ መረጃ አመላክቷል።
Exit mobile version