አዲስ አበባ፣ ግንቦት 17፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ጤና ሚኒስቴር የተጠናከረ የኢቦላ በሽታ መከላከል ቅድመ ዝግጅት ስራዎች እየተከናወኑ ነው አለ፡፡
የዓለም ጤና ድርጅት ባወጣው መግለጫ፤ በዴሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ እና በዩጋንዳ በቡንዲቡግዮ ቫይረስ ዝርያ የሚመጣ የኢቦላ ቫይረስ በሽታ ተከስቷል።
በዚህም እስከ ትናንት ድረስ በሀገራቱ በአጠቃላይ ከ101 በላይ የሚሆኑ በላቦራቶሪ የተረጋገጡ ታማሚዎች እና ከ900 በላይ ንክኪ ያላቸው ተጠርጣሪዎች የህክምና ክትትል ላይ ይገኛሉ።
የኢቦላ ቫይረስ በሽታ ከፍተኛ የስርጭት እና የሞት ምጣኔ ያለው በሽታ መሆኑን የጠቀሰው ጤና ሚኒስቴር፤ እስከዛሬ ድረስ በሀገራችን በኢቦላ ቫይረስ በሽታ የተጠረጠረ ወይም የታመመ ሰው አልተገኘም ብሏል።
ኢትዮጵያ በሽታው ከተገኘባቸው ሀገራት ጋር ቀጥተኛ የድንበር ግንኙነት ባይኖራትም የበሽታውን አደገኛነት በመገንዘብ የወረርሽኙ መከሰት ይፋ ከተደረገበት ጊዜ ጀምሮ የጤና ሚኒስቴር ከኢትዮጵያ የሕብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር የቅድመ መከላከል ስራዎች እየሰራ እንደሆነ አመልክቷል።
በዚህም በሁሉም ዓለም አቀፍ የየብስ መግቢያ እና መውጫ ኬላዎች የልየታ እና የቅኝት ስራዎችን በማጠናከር፣ በዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያዎች የተጠናከረ ክትትል በማድረግ እና የጤና ተቋማትን ዝግጁ በማድረግ እንዲሁም የላቦራቶሪ አቅምን በማሳደግ ላይ በስፋት እየተሰራ ነው ብሏል።
እንዲሁም አስፈላጊው የህክምና ግብአት አቅርቦት ላይ የተጠናከረ የቅድመ ዝግጅት ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝ ሚኒስቴሩ ይፋ አድርጓል።

