Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ኡሁሩ ኬንያታ ለኢትዮጵያ ምርጫ ስኬት ከአፍሪካ ዲፕሎማቶች ጋር መከሩ

አዲስ አበባ፣ ግንቦት 23፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የአፍሪካ ኅብረት የምርጫ ታዛቢ ቡድን መሪና የኬንያ የቀድሞ ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬንያታ መቀመጫቸውን በአዲስ አበባ ካደረጉ የአፍሪካ ዲፕሎማቲክ ማኅበረሰብ ተወካዮች ጋር ተወያይተዋል።

ውይይቱ በዋነኝነት ትኩረቱን ያደረገው በኢትዮጵያ ነገ በሚካሄደው ጠቅላላ ምርጫ ዝግጅት እና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ነው።

የአፍሪካ ኅብረት የፖለቲካ፣ ሰላምና ፀጥታ ጉዳይ ኮሚሽን ባወጣው መረጃ መሠረት፤ ፕሬዚዳንት ኬንያታ ከ37 የአፍሪካ ሀገራት የተውጣጡ 73 የአጭር ጊዜ ታዛቢዎችን ያቀፈ ጠንካራ እና ስብጥሩ የሰፋ ቡድን እየመሩ ይገኛሉ።

ይህ የታዛቢ ቡድን ከፍተኛ ልምድ ያላቸውን የምርጫ ባለሙያዎች፣ የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችን እና ታዋቂ የሲቪል ማኅበረሰብ መሪዎችን አካትቷል።

ልዑኩ በመንግሥት እና በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የተከናወኑ የመጨረሻ ዝግጅቶችን መገምገሙ ታውቋል።

ከ54 ሚሊዮን በላይ መራጮች ድምጽ ለመስጠት በተመዘገቡበት በዚህ ጠቅላላ ምርጫ ሂደቱ ለኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ እድገት ወሳኝ ምዕራፍ ተደርጎ ተወስዷል።

ይህ ለኢትዮጵያውያን የብሔራዊ ጥቅም እና የሉዓላዊነት ጉዳይ የሆነው ምርጫ፤ ሕዝቡ ዲሞክራሲያዊ መብቱን በመጠቀም ሉዓላዊነቱን ለዓለም ማኅበረሰብ የሚያሳይበት አጋጣሚ እንደሚሆን ይጠበቃል።

ለምርጫው የሎጂስቲክስ እና የፀጥታ ዝግጅቶች መጠናቀቃቸውን አረጋግጧል።

በኡሁሩ ኬንያታ የሚመራው የታዛቢ ቡድንም የግልጽነት እና የፍትሃዊነት መርሆዎች መከበራቸውን ለማረጋገጥ በመላ ኢትዮጵያ ተሰማርቶ የድምፅ አሰጣጥ ሂደቱን ይከታተላል።

#ኢትዮጵያ #ኢትዮጵያትመርጣለች #በምርጫብቻ #ፋናዲጂታል #Election #fanadigital #Ethiopia #Ethiopiavotes #Democracy #fanatelevision

Exit mobile version