አዲስ አበባ፣ ግንቦት 25፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) ሁለገብ የጥበብ ሰው አርቲስት ኪዳኔ ምስጋናው ሥርዓተ ቀብር በዛሬው ዕለት በአዲስ አበባ አማኑኤል ቤተክርስቲያን ተፈጽሟል።
አርቲስት ኪዳኔ ባጋጠመው ህመም በህክምና ሲረዳ ቆይቶ ግንቦት 23 ቀን 2018 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት የተለየ ሲሆን÷ ሥርዓተ ቀብሩ ቤተሰቦቹ፣ ጓደኞቹ፣ የሙያ አጋሮቹና አድናቂዎቹ በተገኙበት ነው የተፈጸመው።
አርቲስቱ በሙያው ባገለገለበት ሀገር ፍቅር ቴአትር ቤት ከጠዋቱ 3:00 ሰዓት ጀምሮ የሽኝትና ሻማ የማብራት ሥነ ሥርዓት ተካሂዷል።
ለተለያዩ የቴሌቪዥን ዝግጅቶችና የበዓል ፕሮግራሞች ላይ ባቀረባቸው የጥበብ ስራዎች ድምቀት የነበረው አርቲስት ኪዳኔ÷ በፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን ፋና 80 የውዝዋዜ እና የዳንስ ተሰጥኦ ውድድር ላይ በአማካሪነት በመስራት ሙያዊ አስተዋጽዖ አበርክቷል።
ሁለገቡ ከያኒ አርቲስት ኪዳኔ ምስጋናው ከ2017 ዓ.ም ጀምሮ ህይወቱ እስካለፈበት ቀን ድረስ በአንጋፋው ሀገር ፍቅር ቴአትር ቤት ተዘዋውሮ በሙያው ሀገሩን እና ወገኑን በታማኝነትና በትጋት አገልግሏል።

