አበባ፣ ግንቦት 25፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በአዲስ አበባ ከተማ ዴሞክራሲያዊ እና አሳታፊ በሆነ መልኩ በስኬት ተካሂዷል አለ የአዲስ አበባ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት።
የጋራ ምክር ቤቱ የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ድምጽ አሰጣጥ ሒደት መጠናቀቁን አስመልክቶ ለመገናኛ ብዙሃን መግለጫ ሰጥቷል።
በመግለጫውም ምክር ቤቱ ጠቅላላ ምርጫው ተጀምሮ እስከሚጠናቀቅ ድረስ አስፈላጊውን ክትትል ሲያደርግ እንደነበር አስታውሷል፡፡
የጋራ ም/ቤቱ ሰብሳቢ ማሩ ጃኔ እንዳሉት÷ በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ የመዲናዋ ነዋሪዎች በነቂስ ወጥተው በምርጫው በመሳተፍ የሚፈልጉትን ፓርቲ በነጻነት መርጠዋል፡፡
በምርጫ ሒደቱ ሴቶች፣ ወጣቶች፣ አረጋዊያን፣ አካል ጉዳተኞች በአጠቃላይ የመዲናዋ ነዋሪዎች በፍጹም ጨዋነት በምርጫው በንቃት መሳተፋቸውን ተናግረዋል፡፡
የምርጫ ሒደቱ በከተማዋ ምንም አይነት የጸጥታ መደፍረስም ሆነ የምርጫ ሕግ መጣስ ሳይኖር ፍጹም ሰላማዊ ሆኖ መጠናቀቁን አብራርተዋል።
በመዲናዋ የታየው ስኬታማ የምርጫ ድባብ አዲስ አበባ ሞዴል የዴሞክራሲ ሥርዓት መገንባት እንደምትችል በተግባር ያሳየችበት ነው ሲሉም አጽንኦት ሰጥተዋል፡፡
ምክር ቤቱ ለምርጫው ስኬት ላበረከቱ ለመዲናዋ ነዋሪዎች፣ ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እንዲሁም ለጸጥታ አካላት ምስጋና አቅርቧል።
በቅድስት አባተ

