Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

የገዳ ስርዓት፣ ሀገር በቀል ዴሞክራሲ…

ገዳ ጥንታዊ እና ጥልቅ የአስተዳደር ስርዓት ነው።

የኦሮሞ ህዝብ ለሺህ ዓመታት ሲተዳደርበት የኖረ እና ለዛሬው ትውልድ ያወረሰው ድንቅ ስርዓት።

የገዳ ስርዓት ከተራ አስተዳደራዊ ማዕቀፍ በላይ እንደሆነም ይነገርለታል።

የኦሮሞ ህዝብ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበራዊ እና መንፈሳዊ የህይወት መገለጫም ነውና።

የሌሎች ሀገራትን ዘመናዊ ራስን በራስ የማስተዳደር ፅንሰ-ሀሳብ በብዙ ዘመን የቀደመ፣ ድንቅ ሀገር በቀል ኢትዮጵያዊ የዴሞክራሲ ማሳያ ነው።

የገዳ ስርዓትን ከሌሎች የዴሞክራሲ ስርዓቶች የሚለየው ለእኩልነት ያለው ቦታ እና አሳታፊነቱ ነው።

የኦሮሞን ህዝብ በአምስት የተለያዩ የገዳ ክፍሎች በማደራጀት ስልጣኑ በጥቂቶች እጅ እንዳይሰበሰብ ወይም በጎሳ ግንኙነት ወይም በማህበራዊ አቋም እንዳይወሰን ያደርጋል።

ይህ የረቀቀ መዋቅር ልዩ የሆነና የተዘዋዋሪ የአመራር ስርዓትን ያመቻቻል።

እያንዳንዱ አምስት የገዳ ክፍል በስምንት ዓመት ዑደት ውስጥ የአስተዳደር ካባ የሚይዝበት ዲሞክራሲያዊ ስርዓት ነው ።

ይህ በየጊዜው የሚደረገው የስልጣን ሽግግር የዴሞክራሲያዊ ባህሪይ መገለጫ እና ሁሉን አቀፍ ፍልስፍናነቱን ያረጋግጣል።

ገዳ አስተዳደራዊ ብቻ ሳይሆን የህብረተሰቡን ሁለንተናዊ ደህንነት እና የሞራል ገጽታም ይመለከታል።

ከፖለቲካ ዑደቱ ባሻገር ማህበራዊ ትስስርን የሚያጎለብቱና አለመግባባቶች የሚፈቱበት ብሂልም አለው።

ለትውልድ ተሻጋሪ እንዲሆን፣ ገዳ ባህላዊ ተቋማትን እና ተግባራትንም ያቀፈ ስርዓት ነው።

Exit mobile version