Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የ2019 ረቂቅ በጀት 502 ነጥብ 27 ቢሊየን ብር ሆኖ ቀረበ

አዲስ አበባ፣ ሰኔ 12፣ 2018 (ኤፍ ኤም ሲ) የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ ዛሬ ባካሄደው መደበኛ ስብሰባው የከተማዋን የ2019 ረቂቅ በጀት ጨምሮ በተለያዩ አጀንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔዎችን አሳልፏል።

ካቢኔው በዛሬው የ5ኛ ዓመት 12ኛ መደበኛ ስብሰባ ያሳለፋቸው ውሳኔዎች እንደሚከተው ቀርበዋል፡-

1ኛ –  በገለልተኛ የግል  ተቋም የተጠናዉን የከተማዋን ገቢ  የማመንጨት አቅም ጥናት ላይ ተወያይቶ ጥናቱ ይበልጥ በሁሉም ባለድርሻ አካላት በዉይይት እንዲዳብር አቅጣጫ አስቀምጧል።

2ኛ – የ2019 ዓ.ም  የከተማ አስተዳደሩ የቀጣይ ዓመት ረቂቅ በጀት 502 ነጥብ 27 ቢሊየን ብር ሆኖ ወደ ለከተማው ምክር ቤት እንዲመራ ወስኗል።

ይህ የሀብት ድልድል እና ምደባ በዋናነት የሚከተሉትን መስፈርቶችና ታሳቢዎች መሰረት ያደረገ ነው፦

* የከተማ አስተዳደሩን የልማት ስትራቴጂዎች እና የትኩረት አቅጣጫዎች፤

* ድህነትን ለመቀነስ፣ ዘላቂ የልማት ግቦችን ለማረጋገጥ ፣የነዋሪዉን የልማት ፍላጎትና የአገልግሎት አቅርቦት ለማሳደግ በተለይም  የስራ እድል ፈጠራን ለሚያበረታቱ የመሰረተ ልማት ፕሮጀክቶች (መንገድ፣ ዉሃ፣ መኖሪያ ቤት፣ ፅዳት፣ ትራንስፖርትና የእሳትና ድንገተኛ አደጋ መከላከል) ፣እንዲሁም

* ማህበራዊ አገልግሎቶችን ለማሻሻል ሚና ላላቸዉ ዘርፎች (ትምህርት፣ ጤና እና በዝቅተኛ ገቢ ለሚተዳደሩ የከተማዋ ነዋሪዎች የሚደረግ ድጎማ)።

በዚሁ መሰረት በከተማው አስተዳደር ለማዕከል ሴክተር ተቋማትና ለክፍለ ከተሞች ለመደበኛና ለካፒታል ፕሮጀክቶች ማስፈጸሚያነት ከተደለደለው አጠቃላይ ወጪ ውስጥ፤ ከፍተኛውን ድርሻ የሚይዘው 71 በመቶ ለድህነት ቅነሳና ለዘላቂ ልማት ግቦች ማስፈጸሚያ የተመደበ ሲሆን፣ ቀሪው 29 በመቶ ደግሞ ለአስተዳደራዊ ወጪዎች ተደልድሏል።

3ኛ/ በፍትህ ቢሮ ተዘጋጅቶ በቀረብዉ ፤- የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የመንግስት ሰራተኞች የብቃት መመዘኛ እና ማረጋገጫ ተቋም ስልጠና የተግባር አደረረጃጀት እና አሰራሩን ለመወሰን በተዘጋጀዉ ረቂቅ ደንብ ላይ ተወያይቶ ዉሳኔ አሳልፏል፡፡

4ኛ/ ማዘጋጃ ቤታዊ ይዞታ አገልግሎት ክፍያ ማስፈፀሚያ ረቂቅ ደንብ ተወያይቶ ዉሳኔ አሳልፏል፡፡

5ኛ/ በመሬት ልማት አስተዳደር ቢሮ ተዘጋጅቶ የቀረበ ሀገራዊ ፋይዳ ላላቸዉ ፕሮጀክቶች የቀረበ የመሬት ምደባ ላይ ተወያይቶ ካቢኔዉ ዉሳኔ አሳልፏል፡፡

Exit mobile version