አዲስ አበባ፣ ጥቅምት 2፣ 2013 (ኤፍ ቢ ሲ) ኮሮናቫይረስ በአንዳንድ ቦታዎች ላይ ለ28 ቀናት መቆየት እንደሚችል ጥናት አመላከተ፡፡
ኮቪድ-19ን የሚያስከትለው የኮሮና ቫይረስ ከጉንፋን ቫይረስ በባሰ በገንዘብ ኖቶች፣ በብርጭቆ እና በማይዝግ ብረት ለ28 ቀናት ሊቆይ እንደሚችል ነው የአውስትራሊያ ተመራማሪዎች የተናገሩት፡፡
በሽታውን ለመከላከልም በተደጋጋሚ እጅን በአግባቡ ማጽዳት እንዲሁም የምንጠቀምባቸውን ቁሶች ማጽዳት እንደሚያስፈልግም ገልጸዋል፡፡
የአውስትራሊያ ብሔራዊ የሳይንስ ኤጄንሲ ተመራማሪዎች በሞባይል ስልክ ስክሪን፣ ፕላስቲክ የገንዘብ ኖቶች እና መስታወቶች እና ለስላሳ ይዘት ባላቸው ቁሶች ላይ ቫይረሱ ለ28 ቀናት ሊቆይ እንደሚችል ገልጸዋል፡፡
ቫይረሱ በእነዚህ ቁሶች ላይ በ20 ዲግሪ ሴንቲ ግሬድ የሙቀት መጠን መቆየት ይችላልም ነው ያሉት፡፡
የሙቀት መጠኑ ከፍ ባለ ቁጥር ግን ቫይረሱ የሚቆይባቸው ቀናቶች እያነሱ እንደሚመጡም አስረድተዋል፡፡
ምንጭ፡- አልጀዚራ

