Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ቱሪዝምና ሰላም የማይነጣጠሉ መሆኑን ተገንዝበን ልንሰራ ይገባል- ባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር

አዲስ አበባ ፣ጥቅምት 22፣ 2013 ( ኤፍ.ቢ.ሲ)- ቱሪዘምና ሰላምየማይነጣጠሉ ጉዳዮች መሆናቸውን ተገንዝበን መስራት ይጠበቅብናል ሲሉ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር ዴኤታ ወይዘሮ ቡዜና አብዱልቃድር አስታወቁ ።
የዓለም የቱሪዝም ቀን በኦሮሚያ ክልል ደረጃ በሻሸመኔ ከተማ እየተከበረ ነው ።
በበዓሉ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት ሚኒስትር ዴአታዋ በወቅቱ እንደገለጹት በሀገራችን በሁሉም ክልሎች በርካታ የቱሪዝም ፀጋዎች አሉ÷ ይሁንና ፀጋዎቹን አልምተን ወደ አገልግሎት ማስገባት ላይ ብዙ ስራ ይቀረናል ብለዋል።
በአገር አቀፍ ደረጃ የተደረገው የኢኮኖሚ ማሻሻያ ቱሪዝምን ዋነኛ የትኩረት አቅጣጫ ማድረጉን ተናግረዋል ።
በቱሪዝም የዜጎችን ህይወት ወደ ብልፅግና ለመውሰድ በሁሉም ክልሎች እየተሰራ መሆኑን አመልክተዋል ።
አያይዘውም የኮቨድ 19 ፕሮቶኮልን በመጠበቅ መስህቦችን ማልማትና የጎብኚዎችን ደህንነት መጠበቅ የሁሉም ሥራ ሊሆን ይገባል ብለዋል ።
ቱሪዝምና ሰላም የማይነጣጠሉ ጉዳዮች በመሆናቸው ኦሮሚያን ጨምሮ ሁሉም ክልሎች ለሰላም ቅድሚያ በመስጠት ዘርፉን ማሳደግ እንደሚገባ አስገንዝበዋል ።
የኦሮሚያ ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኅላፊ አቶ ከበደ ደሲሳ በበኩላቸው ÷ የቱሪዝም ዘርፉን ለማሳደግ የመሰረተ ልማቶች ግንባታና መስህቦችን የማሳወቅ ስራ እየተከናወነ መሆኑን ተናግረዋል ።
የአሁኑ የኦሮሚያን እናስተዋውቅ ጉዞም በኮሮና ቫይረስ ክስተት የተጎዳውን የዘርፉን ኢኮኖሚ መልሶ እንዲያገግም ማስቻል ዓላማ ያደረገ መሆኑን ጠቅሰዋል ።
ኮሮና ቫይረስን እየተጠነቀቅን ሰላም የሰፈነባትን ኦሮሚያ በመጉበኘት ቱሪዝምን እናሳድግም ነው ያሉት ።
የምእራብ አርሲ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ አበራ ቡኖም ምእራብ አርሲ የ13 ወር ፀጋ ማሳያ መሆኑን ተናግረዋል ።
የብዙ ሐይቆችና ብሔራዊ ፓርኮች መገኛ የሆነው ዞኑ የሀገሪቱ የቱሪዝም የጀርባ አጥንት ነው ማለታቸውን ኢዜአ ዘግቧል።
#FBC
የዜና ሰዓት ሳይጠብቁ የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬትን ትኩስ እና ሰበር ዜናዎችን በፍጥነት በአጭር የፅሁፍ መልዕክት መልክ በስልክዎ ላይ እንዲደርስዎ ወደ 8111 OK ብለው ይላኩ።
Exit mobile version