አዲስ አበባ፣ ህዳር 3፣ 2013 (ኤፍቢሲ) የቀድሞው የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት በመከላከያ ሠራዊት ላይ የተፈጸመው ክህደት እንዳስቆጣው አስታወቀ።
የቀድሞው የኢትዮጵያ የመከላከያ ሠራዊት አመራሮች ጋዜጣዊ መግለጫ የሰጡ ሲሆን መንግስት ጥሪ ካደረገላቸው ከመከላከያ ሰራዊት ጎን ለውጊያ ለመሠለፍ ዝግጁ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
ህወሓት ከዚህ በፊት የቀድሞ የሠራዊት አባላትን የበታተነ መሆኑን ያስታወሱት አመራሮቹ አሁንም ይህን ዓላማውን እንደገና ለማሳካትና የሥልጣን ጥማቱን ለማርካት መከላከያ ሠራዊት ላይ ጥቃት መፈጸሙን ነው በመግለጫቸው ያስረዱት፡፡
የመከላከያ ሠራዊት ለሀገሩ ሲዋደቅ የቆየና ለሕዝብ የሞተ፣ የደማና የቆሰለ መሆኑን አስታውሰው በሠራዊቱ ላይ የተፈፀመው ጥቃት እጅጉን እንዳስቆጣቸውና ቡድኑ እስከሚደመሰስ ድረስ አብረው ለመዋጋት ዝግጁ መሆናቸውን በመግለጫቸው አረጋግጠዋል።
በአሁን ጊዜ በሁሉም የሀገሪቱ ክፍሎች ከ274 በላይ ቅርንጫፎችን ይዞ በመንቀሳቀስ ላይ የሚገኘው ድርጅቱ በውስጡም ከአንድ ሚሊየን በላይ የሠራዊት አባላት እንዳሉት ከኢፌዴሪ መከላከያ ሰራዊት ገጽ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

