Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

የተመድ የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ በትግራይ ክልል የሚገኙ የኤርትራ ስደተኛ መጠለያ ጣቢያዎችን ጎበኙ

አዲስ አበባ፣ ጥር 22፣ 2013 (ኤፍቢሲ) የተመድ የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ በትግራይ ክልል የሚገኙ የኤርትራ ስደተኛ መጠለያ ጣቢያዎችን ጎበኝተዋል፡፡

የሰላም ሚኒስትር ሙፈሪያት ካሚልም  ኢትዮጵያ ስደተኞች በማኅበራዊ ጉዳዮች እንዲሳተፉ ፖሊሲ በመቅረጽና የተለያዩ ተግባራትን በማከናወን ላይ ትገኛለች ብለዋል።

በጉብኝቱ ላይ የሰላም ሚኒስትር ወይዘሮ ሙፈሪያት ካሚል ጨምሮ ፣የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ዴኤታ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን ፤የስደተኞችና ከስደት ተመላሾች ጉዳይ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር አቶ ተስፋሁን ጎበዛይ ከተመድ ሉዑካን ቡድን ጋር የስደተኛ መጠለያ ጣቢያዎችን ጎብኝተዋል።

በዚህ ወቅት የሰላም ሚኒስትር ወይዘሮ ሙፈሪያት ካሚል  መንግስት የትግራይ ክልልን ሰላምና ጸጥታ በአስተማማኝ ሁኔታ ማስጠበቁን ገልጸዋል።

ሚኒስትሯ አያይዘውም ኢትዮጵያ ስደተኞችን በመቀበልና በማስተናገድ ግንባር ቀደም ሃገር መሆናን አመልክተዋል።

ለማሳያነትም የስደተኞች ደህንነት ተጠብቆ በማኅበራዊ ጉዳዮች እንዲሳተፉ ፖሊሲ በመቅረጽና የተለያዩ ተግባራትን በማከናወን ላይ እንደምትገኝ አስታውቀዋል።

የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር አቶ ዴኤታ ሬድዋን ሁሴን በበኩላቸው ጉብኝቱ የትግራይ አካባቢን ደህንነት  በተመከለተ የሚወጡ የተሳሳቱ መረጃዎችን  ሐሰተኛነት ያረጋገጠ መሆኑን ጠቁመው ሰላምን በማስጠበቅ ረገድ የተከናወነውን ተግባርና አሁናዊ የሰላምና ደህንነት ሁኔታውን ማረጋገጫ የሰጠ ነው ብለዋል።

የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ በማይ አይኒ የኤርትራ ሰደተኞች መጠለያ ካምፕ ስደተኞችን ተዘዋውረው ተመልክተዋል።

ኢትዮጵያ ከ1ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ከተለያዩ አገራት የመጡ ስደተኞችን ተቀብላ ታስተናግዳለች።

ከእነዚህ ውስጥ 1መቶ ሺ የሚሆኑት ኤርትራውያን ስደተኞች ናቸው።

ኢትዮጵያ ውስጥ ከሚገኙት 1 መቶ ሺ ስደተኞች 46ሺ አካባቢ የሚሆኑት ትግራይ ክልል ውስጥ በሚገኙ 4 መጠለያ ጣቢያ ውስጥ ተጠልለው ይገኛሉ።

የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽነር ፊሊፖ ግራንዲ ዛሬ የጎበኙት በርካታ የኤርትራ ስደተኞች የያዘውን መጠለያ መሆኑን ኢዜአ ዘግቧል።

የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤

ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ

ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ

ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን

ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

 

Exit mobile version