አዲስ አበባ፣ ጥር 24፣ 2013 (ኤፍ.ቢ.ሲ) በተለያዩ ባንኮች ተቀጥረው የሚሠሩ የጥበቃ ሰራተኞች በአሠሪና ሠራተኛ አገናኝ ኤጀንሲዎች እየተበዘበዙ መሆኑን ለህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሴቶች፣ ወጣቶችና ማህበራዊ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ ተናገሩ፡
ኮሚቴው በአማራ ክልላዊ መንግሥት በደሴ ከተማና ዙሪያ ባሉ አካባቢዎች የተለያዩ ተቋማት የመስክ ምልከታ አድርጓል፡፡
በምልከታውም በተለያዩ ባንኮች ተቀጥረው የሚሰሩ የጥበቃ ሰራተኞችን ጉልበት የአሠሪና ሠራተኛ አገናኝ ኤጀንሲዎች እየተበዘበዙ መሆኑን በተወካዮቻቸው በኩል ለኮሚቴው አባላት ቅሬታቸውን አሰምተዋል፡፡
የጉልበት ብዝበዛ ደረሰብን የሚሉት የጥበቃ ሠራተኛ ተወካዮች ኤጀንሲዎች የጥበቃ ሠራተኞቹን በቋሚነት ስለማይቀጥሯቸው ከኤጀንሲ ኤጀንሲ በማዘዋወር ያሰሩናል ብለዋል፡፡
ባንኮች ለኤጀንሲዎች የሚከፍሏቸው ሦስት ሺህ አምስት መቶ አራት ብር ቢሆንም ኤጀንሲዎቹ ለጥበቃ ሠራተኞቹ የሚከፍላቸው ግን አንድ ሺህ ስምንት መቶ ብር ብቻ በመሆኑ ለጉልበት ብዝበዛ ተጋልጠናል ሲሉ ጠቁመዋል፡፡
የኤጀንሲው ቀጥሮ ለሚያሰራቸው የጥበቃ ሠራተኞች በቂ የጥበቃ መሣሪያ እንደ ጫማ፣ ካፖርት፣ የዝናብ ልብስና ባትሪ በአግባቡ ስለማያቀርብላቸው እየተቸገሩ መሆኑንም ነው ጨምረው የተናገሩት፡፡
የቡድኑ አስተባባሪ የተከበሩ ወይዘሮ ሙንተሀ ኢብራሂም በኩላቸው በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የወጣው አዋጅ ተግባራዊ አለመሆኑን፣ በኤጀንሲዎች የሚቀጠሩ ሠራተኞች ባለው የቅጥር ሁኔታ ላይ ግልፅ መረጃ የማይሠጣቸው መሆኑን፣ ደመወዛቸው ምን ያህል እንደሆነ፣ ከሚያገኙት ደሞዝ ለጡረታ ምን ያህል እንደቆረጥባቸው፣ ለጡረታ የተቆረጠባቸው ገንዘብ ገቢ ስለመሆኑ የማያውቁ እና ስለመብት እና ግዴታቸው የጠራ መረጃ የማይሰጣቸው እና ኤጀንሲዎቹ በቂ ግንዝቤ ከመስጠት አንፃር ውስንነት እንዳለባቸው ጠቁመዋል፡፡
በደሴ ከተማ የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ መመሪያ የማህበራዊ ምክክሮሽና የሥራ ቦታ ትብብር ባለሙያ አቶ አበበ መለሰ እንደገለጹት ኤጀንሲዎቹ ወንዶችን ለጥበቃ እና ሴቶቹን ደግሞ ለፅዳት ሥራ እንደሚቀጥሯቸው ተናግረዋል፡፡
አንድ ኤጀንሲ የጥበቃ ሠራተኞቹ ለአንድ ወይም ለሁለት ዓመት ቀጥሮ ካሰራቸው በኋላ ሌላው ኤጀንሲ ተወዳድሮ ሲያሸንፍ አግልግሎታቸውን ሳይዝ እንደአዲስ በጊዜያዊነት የሚቀጥራቸው በመሆኑ እንደሚቸገሩ ጠቁመዋል፡፡
አያይዘውም የባንክ ጥበቃ ሠራተኞችን ችግር ለመፍታት ባንኮችስ ምን ያህል ዝግጁ ናቸው ተብሎ ለተነሳላቸው ጥያቄም አቶ አበበ በሰጡት ምላሽ በዲስሪክት ደረጃ ያሉ የባንክ አመራሮች ‹‹ፈፅሙ›› ተብለው የታዘዙትን እንደሚፈጽሙና የኤጀንሲው ማህተም ሳይኖር በፊርማ ብቻ ለሠራተኞቹ ማስጠንቂያ እንደሚሰጡ ተናግረዋል፡፡
አክለውም ኤጀንሲዎቹ ፈቃድ የሚያወጡት አዲስ አበባ በመሆኑ የኤጀንሲ ባለቤቶችን በአካል አግኝቶ ማነጋገርና ችግሩን መፍታት እንዳልተቻለም ነው ለኮሚቴው ያስረዱት፡፡
የቡድኑ አስተባባሪ የተከበሩ ወይዘሮ ሙንተሀ ኢብራሂም ኤጀንሲዎች በሠራተኞች ላይ ከፍተኛ የጉልበት ብዝበዛ እና በላባቸው አላግባብ ተጠቃሚ ናቸው የሚል ከፍተኛ ቅሬታ እየቀረበ ስለሆነ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር ችግሩን መፍታት አስፈላጊ እንደሆነ ማሳሰባቸውን ከህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡
ከፌስቡክ ገፃችን በተጨማሪ ወቅታዊ፣ ትኩስ እና የተሟሉ መረጃዎችን ለማግኘት፡-
የፋና ድረ ገጽ https://www.fanabc.com/ ይጎብኙ፤
ተንቀሳቃሽ ምስሎችን ለማግኘት የፋና ቴሌቪዥን የዩቲዩብ ቻናል https://www.youtube.com/c/fanabroadcastingcorporate/ ሰብስክራይብ ያድርጉ
ፈጣን መረጃዎችን ለማግኘት ትክክለኛውን የፋና ቴሌግራም ቻናል https://t.me/fanatelevision ይቀላቀሉ
ከዚህ በተጨማሪም በትዊተር ገጻችን https://twitter.com/fanatelevision ይወዳጁን
ዘወትር ከእኛ ጋር ስላሉ እናመሰግናለን!

