Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ከንቲባ አዳነች አቤቤ ከተማ አቀፍ የፅዳት ንቅናቄን አስጀመሩ

አዲስ አበባ፣ ጥር 22፣ 2014 (ኤፍ ቢ ሲ) ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ በቂርቆስ ክ/ከተማ በመገኘት ከተማ አቀፍ የፅዳት ንቅናቄውን አስጀመሩ፡፡

እንደሚታወቀው ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ 35ኛውን የአፍሪካ ጉባኤ መሰረት በማድረግ የፅዳት ዘመቻ በመላው ከተማይቱ እንደሚካሄድ ጥሪ ማስተላለፋቸው አይዘነጋም፡፡

ይህንን ጥሪ ተከትሎ ዛሬ በመላው ከተማይቱ የፅዳት ፕሮግራም እየተካሄደ ሲሆን ከንቲባ አዳነች አቤቤ በቂርቆስ ክ/ከተማ በመገኘት ከነዋሪዎች ጋር የፅዳት ፕሮግራሙን በይፋ አስጀምረዋል፡፡

በዚህ ፕሮግራም ላይ ንግግር ያደረጉት ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ እንደተናገሩት የአፍሪካ ጉባኤ ስናስተናግድ በዛ አስቸጋሪ ወቅት አዲስ አበባ ተከባለች ኑ ውጡ ሲባሉ ኢትዮጵያ ስትቸገር አብረናት እንቆማለን ፤ እናታችን ናት ፤ኢትዮጵያን ጥለን ወዴት እንሄዳለን በማለት ፤ ከጎነችን የቆሙት የአፍሪካ ወንድሞቻችን ያለንን አክብሮትና ፍቅር የምንገልፅበት ነው፡፡

በተለይም ይህ ጉባኤ ኢትዮጵያ ጉባኤውን ማዘጋጀት እንደምትችል የራሷን ሰላም በራሷ ማረጋገጥ እንደምትችል ያሳየና የውጪ ሃይሎን ጉዳይ ጣልቃ መግባት ይቅር በማለት በ NoMore ንቅናቄ ከጎናችን በመሆን አጋርነታቸውን ስላሳዩን ለአፍሪካውያን አድናቆታችን የምናሳይበት ነው ብለዋል፡፡

በአፍሪካ ወንድሞቻችን እንኮራለን! በአፍሪካዊነታችንም እንኮራለን ያሉት ከንቲባ አዳነች አቤቤ ፤ ይህ ጉባኤ ለየት የሚያደርገው ዳግም ለአፍሪካ ነፃነት ፋና ወጊነታችንን ያሳየንበት ወቅት መሆኑ ነው፡፡

የፅዳት ንቅናቄው ሳምንቱን ሙሉ በተከታታይ በየእለቱ መካሄዱን እንደሚቀጥል ከንቲባዋ በዚሁ አጋጣሚ መናገራቸውን ከከንቲባ ፅህፈት ቤት ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

Exit mobile version