የፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ዋና ስራ አስፈጻሚ አቶ አድማሱ ዳምጠው በፊርማ ሥነ ስርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር፥ የፋና የስልጠና ማዕከል የሚሰራቸው ስራዎች እውቀትና ልምድ ላይ የተመሰረቱ መሆናቸውን ገልጸው፥ የሚዲያ ስራዎች እውቀትንና ልምድን መሰረት ያደረጉ መሆን እንዳለባቸውም አመላክተዋል።
ከዚህ አኳያ ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ያለውን ሰፊ የስልጠና አቅም ተደራሽ ለማድረግ ከተለያዩ ተቋማት ጋር በመተባበር እንደሚሰራ ሁሉ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ኮሙኒኬሽን ቢሮ ጋር ለመስራት ይህንን ስምምነት መፈራረሙ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ጠቁመው፥ ስልጠናው ሙያተኛው የበለጠ እውቀትና ልምድ ላይ የተመሰረተ ስራ እንዲያከናውን ለማድረግ የሚያስችል በመሆኑ ስምምነቱን በሙሉ ኃላፊነት የምንተገብረው ይሆናል ብለዋል።
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኮሙኒኬሽን ቢሮ ኃላፊ አቶ ዮናስ ዘውዴ በበኩላቸው፥ ከዚህ በፊት በተለምዶና በልምድ ሲሰሩ ከነበሩ አሰራሮች ወጣ ብሎ፥ ሳይንስን መሰረት ያደረጉና ልምድንም ግምት ውስጥ ያሰገቡ የኮሙኒኬሽን መንገዶችና እሳቤዎች መሳለጥ አለባቸው ከሚል ብርቱ ሀሳብ የተነሳ ይህንን ውል ልንፈራረም ችለናል ነው ያሉት።
አያይዘውም አገራችን የጀመረችውና እያለፍንበት ያለው የሪፎርም አስተሳሰብና አመለካከት ከዳር እንዲደርስ ሙያና ሙያተኛ መገናኘት ሲችል ብቻ ነው ያሉት አቶ ዮናስ፥ ይህንንም ለመተግበር ከተማችን የሚያስፈልጋት የኮሙኒኬሽን ባለሙያ የሰለጠነ፣ ዓለማችን የደረሰችበትን ቴክኖሎጂ በእውቀትና በብቃት የሚጠቀም መሆን አለበት ብለን ስለምናምን ነው ይህንን የስልጠና ውል ስምምነት የተፈራረምነው ብለዋል።
በዳንኤል ሙሉ

