Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

በመላ ሃገሪቱ ትምህርት ቤቶች እንዲዘጉ፣ ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎችና ትላልቅ ስብሰባዎች እንዳይካሄዱ ተወሰነ

አዲስ አበባ ፣ መጋቢት 7 ፣ 2012 (ኤፍ ቢ ሲ) ከዛሬ ጀምሮ ትምህርት ቤቶች ስፖርታዊ እንቅስቃሴዎችና ትላልቅ ስብሰባዎች በመላ ሃገሪቱ ለ15 ቀናት እንደሚዘጉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ ገለፁ።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ዛሬ በፅህፈት ቤታቸው በሰጡት መግለጫ በዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎች ባሉበት ሆነው አስፈላጊው ክትትል ይደረግላቸዋል ብለዋል።

ከዚህ ጋር ተያይዞም የሳይንስ እና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስቴር በዩኒቨርሲቲዎች ቅጥር ግቢዎችና በተማሪዎች ማደሪያ ክፍሎች ለተማሪዎቹ ለየኮርሶቹ የሚያስፈልጉ ግብዓቶችን በኢንተርኔት የሚያደርስበት ስርዓት እየተቀየሰ እንደሚገኝ ጠቁመዋል።

በመግለጫቸው አነስተኛ ስብሰባዎች በጤና ሚኒስቴር እውቅና እና ክትትል ሊደገፉ እንደሚገባም ገልጸዋል።

ግብአትን በተመለከተ ሳሙና እና አልኮልን ጨምሮ ሌሎች የንፅህና መጠበቂያዎች በስፋት እንደሚሰራጩም አስታውቀዋል።

እነዚህን የንፅህና መጠበቂያዎች ሰዎች በቀላሉ እንዲያገኟቸው በተለያዩ አካባቢዎች እንዲቀመጡ ይደረጋልም ነው ያሉት።

ለዚህ እንዲረዳም እነዚህን ግብዓቶች አስፈላጊ በሆኑባቸው ስፍራዎች እንዲሰራጩ በጀት እንደሚመደብም አስረድተዋል።

የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስቴርም በእነዚህ ቁሳቁስና ግብዓቶች ላይ የዋጋ ጭማሪ የሚያደርጉ አካላትን በመቆጣጠር እርምጃ ይወስዳልም ነው ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ።

የጤና ሚኒስቴር በአረጋውያን ክብካቤ ማዕከላት ክትትል ያደርጋል ያሉት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፥ በጎ ፈቃደኞች ቫይረሱን የመከላከልና የግንዛቤ ማስጨበጥ ስራዎች እንዲሰሩም ጠይቀዋል።

ትራንስፖርትን በተመለከተም በህዝብ ትራንስፖርት ላይ ያለውን መጨናነቅ ለመቀነስ የመንግስት ተሽከርካሪዎች ድጋፍ እንደሚያደርጉና በርካታ ተሽከርካሪ ያላቸው የግል ኩባንያዎች ትብብር እንዲያደርጉም ነው የጠየቁት።

የሃይማኖት ተቋማትን በተመለከተም ምዕመናን የሚሰበሰቡባቸውን ሁኔታዎች በጥንቃቄ ቢመለከቱ የሚል ምክር ሃሳብ አቅርበዋል።

በተጨማሪም ብሄራዊ የንጽህና አጠባበቅና መከላከያ መንገዶችን የሚያስገነዝብና የሚተገብር ንቅናቄ በመንግስት ተቋማት ዘንድ እንደሚጀመር ጠቅሰው፥ መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማትና ህብረተሰቡ ተግባራዊ ማድረግ እንደሚኖርባቸው አውስተዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሁሉም ሰው ተረጋግቶ ከጤና ሚኒስቴር መረጃዎችን እንዲያገኝ፣ የእጅ ንጽህናን በአግባቡ እንዲጠብቅ እና የጤና ሚኒስቴርን መመሪያ በመከተል ከአላስፈላጊ አካላዊ ንክኪ እንዲቆጠብም አሳስበዋል።

ትኩስ መረጃዎችን በፍጥነት ለማግኘት የቴሌግራም ገፃችንን ሰብስክራይብ ያድርጉ!
https://t.me/fanatelevision

Exit mobile version