አዲስ አበባ፣ መሰከረም 29፣ 2016 (ኤፍ ቢ ሲ) ሁሉም ኢትዮጵያውያን ሀገራችሁ ያላትን ሃብት ማየት፣ ማውጣት፣ ማስተዋወቅ እና ማገልገል ይጠበቅባችኋል ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ገለጹ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማህበራዊ ትስስር ገጻቸው ባሰፈሩት ሃሳብ፥ ብዙ ታሪክ፣ ቅርስ፣ ባህል፣ የተፈጥሮ ስጦታዎች፣ አዕዋፍ፣ የዱር አራዊት እና ሊጎበኙ የሚችሉ ድንቅ ሁነቶች እንዳሉን ግምት ውስጥ በማስገባት ከኢኮኖሚው ዘርፍ ዋና ምሦሦዎች አንዱ የቱሪዝም ዘርፉ ነው ብለዋል።
ዛሬ የተከፈተው ሀገር አቀፍ የቱሪዝምና ሆስፒታሊቲ አውደ ርዕይ ጎብኚዎች ኢትዮጵያን ምቹ መዳረሻ የሚያደርጋትን በናሙና እንዲያዩ ዕድል እንደሚሰጥም ነው የገለጹት።
ያለንን ዐቅም ለማውጣት፣ ኢትዮጵያን የብዙ ውበቶችና ግኝቶች መዳረሻ አድርጎ ለማስተዋወቅና ለማገልገል ሁሉም ኢትዮጵያውያን ሀገራችሁ ያላትን ሀብት ማየት፣ ማውጣት፣ ማስተዋወቅና ማገልገል ይጠበቅባችኋል ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።