Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ቻይና ከኢትዮጵያ ጋር ያላት አጋርነት ቀጣይነት ባለው ትብብር መጠናከር እንዳለበት አስታወቀች

አዲስ አበባ፣ ታሕሣሥ 10፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) ቻይና ከኢትዮጵያ ጋር ያላት አጋርነት ቀጣይነት ባለው ትብብር መጠናከር እንዳለበት በአፍሪካ ቀንድ የቻይና ልዩ መልዕክተኛ ዡ ቢንግ ገለጹ፡፡

የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጌዲዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር) በአፍሪካ ቀንድ የቻይና ልዩ መልዕክተኛ ዡ ቢንግ ጋር በሁለትዮሽ፣ አህጉራዊና ዓለም አቀፋዊ ጉዳዮች ላይ መክረዋል፡፡

ጌዲዮን (ዶ/ር) በውይይታቸው ወቅት እንዳሉት፥ የኢትዮ-ቻይና ሁለንተናዊ ስትራቴጂካዊ አጋርነት ጠንካራ እና የማይናወጥ ነው፡፡

ኢትዮጵያ ቀጣናዊ ሰላምና መረጋጋትን ለማስፈን በምታደርገው እንቅስቃሴ ቻይና ቀጣይነት ያለው ድጋፍ እንድታደርግም መጠየቃቸውን ከሚኒስቴሩ ያገኘነው መረጃ ያመላክታል።

በቻይና-አፍሪካ ትብብር መድረክ (ፎካክ) ማዕቀፍ ከተቀመጡት ዓላማዎች ጋር ኢትዮጵያ የኢኮኖሚ ማሻሻያ እና የአረንጓዴ ኢኮኖሚ ስትራቴጂዋን እንዳናበበች አስምረውበታል።

አምባሳደር ዙ ቢንግ፥ በኢትዮጵያና በቻይና መካከል ባለው የሁለትዮሽ ግንኙነት ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሱ ስኬቶችን በመግለጽ፤ አጋርነቱን ቀጣይነት ባለው የትብብር ጥረት ማጠናከር ስላለው የጎላ ሚና አብራርተዋል፡፡

Exit mobile version