Site icon Welcome to Fana Media Corporation S.C

ድርጅቱ በቀን ከ1 ሚለዮን በላይ ሰዎችን እያጓጓዘ ነው

አዲስ አበባ፣ ጥር 6፣ 2017 (ኤፍ ኤም ሲ) በአዲስ አበባ ከተማ በየቀኑ በምልልስ ከ1 ነጥብ 1 ሚሊየን በላይ የሆኑ ዜጎችን እያጓጓዘ መሆኑን የአዲስ አበባ ከተማ አውቶቡስ አገልግሎት ድርጅት አስታወቀ።

የድርጅቱ ዋና ስራ አስፈጻሚ አካሉ አሰፋ ለፋና ሚዲያ ኮርፖሬሽን እንዳሉት÷ ከሌሊቱ 11፡00 ሰዓት እስከ ምሽቱ 4 ሰዓት ድረስ በ988 አውቶቡሶች መደበኛ አገልግሎት እየተሰጠ ነው።

ባለፈው ዓመት በቀን 600 ሺህ ህዝብ በምልልስ ሲስተናገድ እንደነበር አስታውሰው፤ በተያዘው ዓመት የምልልስ አቅምን በማሳደግ ከ1 ነጥብ 1 ሚሊየን በላይ ማድረስ መቻሉን ጠቁመዋል።

የከተማ አውቶቡስ አገልግሎት ድርጅት በ182 መስመሮች አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን አንስተው፤ ባለፉት 6 ወራትም በምልልስ ለ198 ሚሊየን ሰዎች አገልግሎት መሰጠቱን ተናግረዋል ።

ድርጅቱ የመዲናዋን 30 በመቶ የትራንስፖርት ድርሻ ይሸፍናል ያሉት ዋና ስራ አስፈጻሚው የተማሪ እና ሌሎች አገልግሎቶችን ጨምሮ በ1 ሺህ 140 አውቶቡሶች ለከተማው ህዝብ አገልግሎት እየሰጠ መሆኑን ገልጸዋል።

ድርጅቱ ባለፉት 6 ወራት ውስጥ የዕቅዱን 90 በመቶ ማሳካቱን ጠቅሰው፤ አሰራሩን፣ ቴክኖሎጂውን እና አደረጃጀቱን በማዘመን ከነበሩበት ችግሮች በመውጣት የተሻለ አገልግሎት ለመስጠት መዘጋጀቱን ተናግረዋል፡፡

በመሳፍንት እያዩ

Exit mobile version